YouVersion Logo
Search Icon

ማቴዎስ 3

3
የመጥምቁ ዮሐንስ ስብከት
3፥1-12 ተጓ ምብ – ማር 1፥3-8ሉቃ 3፥2-17
1በዚያን ወራት መጥምቁ ዮሐንስ በይሁዳ ምድረ በዳ እየሰበከ መጣ። 2ስብከቱም፣ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ” የሚል ነበር። 3በነቢዩ በኢሳይያስ እንዲህ ተብሎ የተነገረለት እርሱ ነው፤
“በምድረ በዳ፣
‘የጌታን መንገድ አዘጋጁ፤
ጐዳናውንም አስተካክሉ’ እያለ የሚጮኽ ድምፅ።”
4የዮሐንስ ልብስ የግመል ጠጕር ሲሆን፣ ወገቡንም በጠፍር ይታጠቅ ነበር፤ ምግቡም አንበጣና የበረሓ ማር ነበር። 5ከኢየሩሳሌም፣ ከመላው ይሁዳና በዮርዳኖስ ዙሪያ ካለው አገር ሁሉ ሰዎች ወደ ዮሐንስ ይጐርፉ፣ 6ኀጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ በእርሱ እጅ ይጠመቁ ነበር።
7ብዙ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ወደሚያጠምቅበት ስፍራ ሲመጡ ባየ ጊዜ እንዲህ አላቸው፤ “እናንት የእፉኝት ልጆች! ለመሆኑ ከሚመጣው ቍጣ እንድታመልጡ ማን መከራችሁ? 8ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አፍሩ፤ 9‘አብርሃም አባት አለን’ በማለት ራሳችሁን አታታልሉ፤ እግዚአብሔር ከእነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሣ ይችላል እላችኋለሁና። 10እነሆ፤ ምሣር የዛፎችን ሥር ሊቈርጥ ተዘጋጅቷል፤ መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል።
11“እኔ ለንስሓ በውሃ አጠምቃችኋለሁ፤ ነገር ግን ጫማውን መሸከም የማይገባኝ፣ ከእኔ የሚበልጥ ኀያል ከእኔ በኋላ ይመጣል። እርሱም በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል። 12መንሹ በእጁ ነው፤ ዐውድማውን ያጠራል፤ ስንዴውን በጐተራ ይከትታል፤ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል።”
የኢየሱስ መጠመቅ
3፥13-17 ተጓ ምብ – ማር 1፥9-11ሉቃ 3፥2122ዮሐ 1፥31-34
13በዚያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ለመጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ። 14ዮሐንስ ግን፣ “ይህማ አይሆንም፤ እኔ ባንተ መጠመቅ ሲያስፈልገኝ እንዴት አንተ ወደ እኔ ትመጣለህ?” ብሎ ተከላከለ።
15ኢየሱስም፣ “ግድ የለም ፍቀድልኝ፤ ይህን በማድረግ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና” አለው፤ ዮሐንስም በነገሩ ተስማማ።
16ኢየሱስም እንደ ተጠመቀ ከውሃው ወጣ፤ ወዲያውኑም ሰማይ ተከፍቶ የእግዚአብሔር መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድበት አየ። 17እነሆ፤ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወድደው ልጄ ይህ ነው” የሚል ድምፅ ከሰማይ ተሰማ።

Currently Selected:

ማቴዎስ 3: NASV

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in

YouVersion uses cookies to personalize your experience. By using our website, you accept our use of cookies as described in our Privacy Policy