YouVersion Logo
Search Icon

ኢሳይያስ 40

40
የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚያጽናና ቃል
1አጽናኑ፤ ሕዝቤን አጽናኑ፤
ይላል አምላካችሁ።
2ለኢየሩሳሌም አለዝባችሁ ንገሯት፤
ዐውጁላትም፤
በባርነት ያገለገለችበት ዘመን አብቅቷል፤
የኀጢአቷም ዋጋ ተከፍሏል፤
ስለ ኀጢአቷ ሁሉ ከእግዚአብሔር እጅ
ሁለት ዕጥፍ ተቀብላለች።
3የዐዋጅ ነጋሪ ድምፅ እንዲህ ይላል፤
የእግዚአብሔርን መንገድ፣
በምድረ በዳ አዘጋጁ፤
ለአምላካችን አውራ ጐዳና፣
በበረሓ አስተካክሉ።
4ሸለቆው ሁሉ ከፍ ይላል፤
ተራራውና ኰረብታው ሁሉ ዝቅ ይላል፤
ወጣ ገባው ምድር ይስተካከላል፤
ሰርጓጕጡም ሜዳ ይሆናል።
5 የእግዚአብሔርም ክብር ይገለጣል፤
ሰው ሁሉ በአንድነት ያየዋል፤
የእግዚአብሔር አፍ ይህን ተናግሯልና።”
6ድምፅም፣ “ጩኽ” አለኝ፤
እኔም፣ “ምን ብዬ ልጩኽ?” አልሁ።
“ሰው ሁሉ እንደ ሣር ነው፤
ክብሩም ሁሉ እንደ ሜዳ አበባ ነው።
7ሣሩ ይደርቃል፤ አበባውም ይረግፋል፤
የእግዚአብሔር እስትንፋስ ነፍሶበታልና፤
ሕዝቡ በርግጥ ሣር ነው።
8ሣሩ ይደርቃል፤ አበባውም ይረግፋል፤
የአምላካችን ቃል ግን ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል።”
9አንተ ለጽዮን የምሥራችን የምትነግር፤
ከፍ ወዳለው ተራራ ውጣ፤
አንተ ለኢየሩሳሌም ብሥራት የምትነግር፣#40፥9 ወይም፣ ጽዮን ሆይ፤ የምሥራቹን የምታበሥሪ፣ ወደ ረዥም ተራራ ላይ ውጪ ወይም የምሥራቹን የምታበሥሪ ኢየሩሳሌም ሆይ
ድምፅህን ከፍ አድርገህ ጩኽ።
ከፍ አድርገው፤ አትፍራ፤
ለይሁዳም ከተሞች፣
“እነሆ፤ አምላካችሁ!” በል።
10እነሆ፤ጌታ እግዚአብሔር በኀይል
ይመጣል፤
ክንዱ ስለ እርሱ ይገዛል።
እነሆ፤ ዋጋው ከእርሱ ጋር ነው፤
የሚከፍለውም ብድራት አብሮት አለ።
11መንጋውን እንደ እረኛ ያሰማራል፤
ጠቦቶቹን በክንዱ ይሰበስባል፤
በዕቅፉም ይይዛቸዋል፤
የሚያጠቡትንም በጥንቃቄ ይመራል።
12ውሆችን በዕፍኙ የሰፈረ፣
ሰማያትን በስንዝሩ የለካ፣
የምድርን ዐፈር በመስፈሪያ ሰብስቦ የያዘ፣
ተራሮችን በሚዛን፣
ኰረብቶችንም በመድሎት የመዘነ ማነው?
13 የእግዚአብሔርን መንፈስ የተረዳ፣
አማካሪውስ ሆኖ ያስተማረው ማነው?
14ዕውቀት ለማግኘት እግዚአብሔር ማንን አማከረ?
ትክክለኛውንስ መንገድ ማን አስተማረው?
ዕውቀትን ያስተማረው፣
የማስተዋልንም መንገድ ያሳየው ማን ነበር?
15እነሆ፤ አሕዛብ በገንቦ ውስጥ እንዳለች ጠብታ ናቸው፤
በሚዛን ላይ እንዳለ ትቢያ ይቈጠራሉ፤
ደሴቶችንም እንደ ደቃቅ ዐፈር ይመዝናቸዋል።
16ሊባኖስ ለመሠዊያ እሳት አትበቃም፤
የእንስሶቿም ቍጥር ለሚቃጠል መሥዋዕት ያንሳል።
17አሕዛብ ሁሉ በፊቱ እንደ ኢምንት ናቸው፤
ከምንም የማይቈጠሩ መና ናቸው።
18እንግዲህ፣ እግዚአብሔርን ከማን ጋር ታወዳድሩታላችሁ?
ከየትኛውስ ምስል ጋር ታነጻጽሩታላችሁ?
19የተቀረጸውንማ ምስል ባለ እጅ ይቀርጸዋል፤
ወርቅ አንጥረኛም በወርቅ ይለብጠዋል፤
የብር ሰንሰለትም ያበጅለታል።
20እንዲህ ያለውን መባ ማቅረብ የማይችል ምስኪን ድኻ፣
የማይነቅዝ ዕንጨት ይመርጣል፤
የማይወድቅ ምስልን ለማቆምም፣
ታዋቂ ባለሙያ ይፈልጋል።
21አላወቃችሁምን?
አልሰማችሁምን?
ከጥንት አልተነገራችሁምን?
ምድር ከተመሠረተች ጀምሮ አላስተዋላችሁምን?
22እርሱ ከምድር ክበብ በላይ በዙፋን ላይ ይቀመጣል፤
ሕዝቦቿም እንደ አንበጣ ናቸው።
ሰማያትን እንደ ድባብ ይዘረጋቸዋል፤
እንደ መኖሪያ ድንኳንም ይተክላቸዋል።
23አለቆችን ኢምንት፣
የዚህን ዓለም ገዦች እንዳልነበሩ ያደርጋቸዋል።
24ተተክለው ምንም ያህል ሳይቈዩ፣
ተዘርተው ምንም ያህል ሳይሰነብቱ፣
ገና ሥር መስደድ ሳይጀምሩ
አነፈሰባቸው፤ እነርሱም ደረቁ፤
ዐውሎ ነፋስም እንደ ገለባ ጠራርጎ ወሰዳቸው።
25ቅዱሱ፣ “ከማን ጋር ታወዳድሩኛላችሁ?
የሚስተካከለኝስ ማን አለ?” ይላል።
26ዐይናችሁን አንሡ፤ ወደ ሰማይ ተመልከቱ፤
እነዚህን ሁሉ የፈጠረ ማን ነው?
የከዋክብትን ሰራዊት አንድ በአንድ የሚያወጣቸው፣
በየስማቸው የሚጠራቸው እርሱ ነው።
ከኀይሉ ታላቅነትና ከችሎታው ብርታት የተነሣ፣
አንዳቸውም አይጠፉም።
27ያዕቆብ ሆይ፤ ለምን እንዲህ ትላለህ?
እስራኤል ሆይ፤ ለምን እንዲህ ትናገራለህ?
“መንገዴ ከእግዚአብሔር ተሰውራለች፤
ፍርዴም በአምላኬ ቸል ተብላለች” ለምን ትላለህ?
28አታውቅምን?
አልሰማህምን?
እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፣
የምድር ዳርቻ ፈጣሪ ነው።
አይደክምም፤ አይታክትም፤
ማስተዋሉም በማንም አይመረመርም።
29ለደከመው ብርታት ይሰጣል፤
ለዛለው ጕልበት ይጨምራል።
30ወጣቶች እንኳ ይደክማሉ፤ ይታክታሉም፤
ጐበዛዝትም ተሰናክለው ይወድቃሉ።
31 እግዚአብሔርን ተስፋ የሚያደርጉ ግን፣
ኀይላቸውን ያድሳሉ፤
እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤
ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፤
ይሄዳሉ፤ አይደክሙም።

Currently Selected:

ኢሳይያስ 40: NASV

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in

YouVersion uses cookies to personalize your experience. By using our website, you accept our use of cookies as described in our Privacy Policy