የሐዋርያት ሥራ 24:1-16
የሐዋርያት ሥራ 24:1-16 አማ2000
በአምስተኛውም ቀን ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ ከመምህራኑና ጠርጠሉስ ከሚባል አንድ ጠበቃ ጋር ወረደ፤ ጳውሎስንም በአገረ ገዢው ዘንድ ከሰሱት። ጳውሎስም በቀረበ ጊዜ ጠርጠሉስ እንዲህ እያለ ይከስሰው ጀመረ፤ “ክቡር ፊልክስ ሆይ፥ በዘመንህ ብዙ ሰላምን አግኝተናል፤ በጥበብህም በየጊዜው በየሀገሩ የሕዝቡ ኑሮ የተሻሻለ ሆኖአል፤ ሥርዐትህንም በሁሉ ዘንድ ስትመሰገን አግኝተናታል። ነገር ግን ነገር እንዳላበዛብህ በአጭሩ ትሰማኝ ዘንድ እለምንሃለሁ። ይህን ሰው ሲሳደብና ወንጀል ሲሠራ፥ አይሁድንም ሁሉ በየሀገሩ ሲያውክ፥ ናዝራውያን የተባሉት ወገኖች የሚያስተምሩትንም ክህደት ሲያስተምር አግኝተነዋል። ቤተ መቅደስንም ሊያረክስ ሲሞክር ያዝነው፤ እንደ ሕጋችንም ልንፈርድበት ፈልገን ነበር። ነገር ግን የሻለቃው ሉስዮስ መጥቶ በብዙ ጭንቅ ከእጃችን ነጥቆ ወደ አንተ ላከው። ከሳሾቹንም ወደ አንተ እንዲመጡ አዘዛቸው፤ የከሰስንበትንም ነገር ሁሉ መርምረህ ከእርሱ ልትረዳ ትችላለህ።” አይሁድም፥ “እውነት ነው፤ እንዲሁ ነው” ብለው መለሱ። ሀገረ ገዢውም እንዲናገር ጳውሎስን ጠቀሰው፤ ጳውሎስም እንዲህ አለ፥ “ከብዙ ዘመን ጀምሮ የዚህ ሕዝብ አስተዳዳሪ እንደ ሆንህ አውቃለሁ፤ ጠባያቸውንም ታውቃለህ። አሁንም ደስ እያለኝ ክርክሬን አቀርባለሁ። እሰግድ ዘንድ ወደ ኢየሩሳሌም ከወጣሁ ዐሥራ ሁለት ቀን እንደማይሆን ልታውቀው ትችላለህ፤ በምኵራብ ቢሆን፥ በቤተ መቅደስም ቢሆን፥ በከተማም ቢሆን ሕዝብን ሳውክ፥ ከማንም ጋር ስከራከር አላገኙኝም። በሚከስሱኝ ሁሉ በፊትህ ማስረጃ ማቅረብ አይችሉም። ነገር ግን ይህን አረጋግጥልሃለሁ፤ እኔ በሕግ ያለውን፥ በነቢያትም የተጻፈውን ሁሉ አምኜ እነርሱ ክህደት ብለው በሚጠሩት ትምህርት የአባቶችን አምላክ አመልከዋለሁ። እነርሱም ለጻድቃንና ለኃጥኣን የሙታን ትንሣኤ ይሆን ዘንድ እንደሚጠብቁ ለእኔም እንዲሁ በእግዚአብሔር ዘንድ ተስፋ አለኝ። እንዲሁ እኔም በእግዚአብሔርና በሰው ፊት ሁልጊዜ የማታወላውል ሕሊና ትኖረኝ ዘንድ እጋደላለሁ።

