መጽሐፈ ኢያሱ ወልደ ነዌ 6:20-27
መጽሐፈ ኢያሱ ወልደ ነዌ 6:20-27 አማ2000
ሕዝቡም ጮኹ፥ ካህናቱም ቀንደ መለከቱን ነፉ፤ ሕዝቡም የቀንደ መለከቱን ድምፅ በሰሙ ጊዜ ታላቅ ጩኸት ጮኹ፤ ቅጥሩም ወደቀ፤ ሕዝቡም ሁሉ ወደ ከተማዪቱ ገቡ፤ ሁሉም ወደ ፊታቸው ወደ ከተማዪቱ ሮጡ፤ ከተማዪቱንም እጅ አደረጉ። ኢያሱም ከተማዋን፥ በከተማዪቱም ውስጥ የነበሩትን ሁሉ፥ ከወንድ እስከ ሴት፥ ከሕፃን እስከ ሽማግሌ፥ ከበሬ እስከ በግና እስከ አህያ በሰይፍ ስለት ፈጽሞ አጠፋ። ኢያሱም ምድሪቱን የሰለሉ ሁለቱን ሰዎች፥ “ወደ ዘማዪቱ ቤት ግቡ፤ ከዚያም ሴቲቱንና ያላትን ሁሉ እንደማላችሁላት አውጡ” አላቸው። እነዚያም ከተማዪቱን የሰለሉ ሁለቱ ጐልማሶች ወደ ዘማዪቱ ረዓብ ቤት ገብተው ረዓብን፥ አባቷንና እናቷን፥ ወንድሞችዋንም፥ ያላትንም ሁሉ፥ ቤተ ዘመዶችዋንም ሁሉ አወጡአቸው፤ ከእስራኤልም ሰፈር በውጭ አስቀመጡአቸው። ከተማዪቱንም፥ በእርስዋም የነበረውን ሁሉ በእሳት አቃጠሉ፤ ነገር ግን ብሩንና ወርቁን፥ የናሱንና የብረቱንም ዕቃ በእግዚአብሔር ግምጃ ቤት ውስጥ አገቡ። ኢያሪኮን ሊሰልሉ ኢያሱ የላካቸውንም መልእክተኞች ስለ ሸሸገች ዘማዊቱን ረዓብን፥ የአባቷንም ቤተ ሰብ፥ ያላትንም ሁሉ ኢያሱ አዳናቸው፤ እርስዋም በእስራኤል መካከል እስከ ዛሬ ድረስ ተቀምጣለች። በዚያችም ቀን ኢያሱ፥ “ይህችን ከተማ ኢያሪኮን ለመሥራት የሚነሣ ሰው በእግዚአብሔር ፊት ርጉም ይሁን፤ መሠረቷን በበኵር ልጁ የሚጥል፥ በሮችዋንም በታናሹ ልጁ የሚያቆም ርጉም ይሁን” ብሎ ማለ። እግዚአብሔርም ከኢያሱ ጋር ነበረ፤ ስሙም በምድር ሁሉ ላይ ደረሰ።

