ኦሪት ዘፍጥረት 14:12-24
ኦሪት ዘፍጥረት 14:12-24 አማ2000
እነርሱም የአብራምን የወንድም ልጅ ሎጥንና ገንዘቡን ይዘው ሄዱ። እርሱ በሰዶም ይኖር ነበርና። ከአመለጡትም አንድ ሰው መጣ፤ ለዕብራዊው ለአብራምም ነገረው፤ እርሱም የኤስኮል ወንድምና የአውናን ወንድም በሆነ በአሞራዊው የመምሬ ዛፍ ይኖር ነበር፤ እነዚያም ከአብራም ጋር ቃል ኪዳን ገብተው ነበር። አብራምም የወንድሙ ልጅ ሎጥ እንደ ተማረከ በሰማ ጊዜ ወገኖቹንና ቤተሰቦቹን ሁሉ ቈጠራቸው፤ እነርሱም ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ሆኑ፤ እስከ ዳን ድረስ ተከትሎ አሳደዳቸው። እርሱም ከብላቴኖቹ ጋር በሌሊት ደረሰባቸው፤ መታቸውም፤ በደማስቆ ግራ እስካለችውም እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። የሰዶምን ፈረሶች ሁሉ አስመለሰ፤ ደግሞም የወንድሙን ልጅ ሎጥንና ንብረቱን፥ ሴቶችንና ሕዝቡንም አስመለሰ። ኮሎዶጎሞርንና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ነገሥታት ወግቶ ከተመለሰም በኋላ የሰዶም ንጉሥ የንጉሥ ሜዳ በሆነ በሴዊ ሸለቆ ሊቀበለው ወጣ። የሳሌም ንጉሥ መልከ ጼዴቅም እንጀራንና የወይን ጠጅን አወጣ፤ እርሱም የልዑል እግዚአብሔር ካህን ነበረ። አብራምንም ባረከው፤ “አብራም ሰማይንና ምድርን ለፈጠረ ለልዑል እግዚአብሔር የተባረከ ነው፤ ጠላቶችህን በእጅህ የጣለልህ ልዑል እግዚአብሔርም ቡሩክ ነው” አለው። አብራምም ከሁሉ ዐሥራትን ሰጠው። የሰዶም ንጉሥም አብራምን፥ “ሰዎቹን ስጠኝ፤ ፈረሶቹን ግን ለአንተ ውሰድ” አለው። አብራምም የሰዶምን ንጉሥ አለው፥ “ሰማይንና ምድርን ወደ ፈጠረ ወደ ልዑል እግዚአብሔር እጄን ከፍ አደርጋለሁ፤ አንተ፦ አብራምን ባለጠጋ አደረግሁት እንዳትል፥ ከአንተ ገንዘብ ሁሉ ፈትልም ቢሆን፥ የጫማ ማዘቢያም ቢሆን እንዳልወስድ፥ ብላቴኖች ከበሉት እህልና ከእኔ ጋር ከመጡት ድርሻ በቀር፥ አውናን፥ ኤስኮልም፥ መምሬም እነርሱ ድርሻቸውን ይውሰዱ።”

