መዝሙረ ዳዊት 78:1-20

መዝሙረ ዳዊት 78:1-20 መቅካእኤ

ሕዝቤ ሆይ፥ ሕጌን አድምጡ፥ ጆሮአችሁንም ወደ አፌ ቃል አዘንብሉ። አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፥ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም እንቆቅልሽ እናገራለሁ። የሰማነውንና ያወቅነውን፥ አባቶቻችንም የነገሩንን፥ ከልጆቻቸው አንሰውረውም፥ ለሚመጣውም ትውልድ የጌታን ምስጋናና ኃይሉን ያደረገውንም ተኣምራት እንናገራለን። ለልጆቻቸው ያስታውቅ ዘንድ ለአባቶቻችን ያዘዘውን ምስክር በያዕቆብ አቆመ፥ በእስራኤልም ሕግን ሠራ፥ የሚመጣ ትውልድ የሚወለዱም ልጆች ያውቁ ዘንድ፥ ተነሥተው ለልጆቻቸው እንዲናገሩ ነው፥ ተስፋቸውን በእግዚአብሔር እንዲያደርጉ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ እንዳይረሱ፥ ትእዛዙንም እንዲጠብቁ፥ እንደ አባቶቻቸው እንዳይሆኑ ዐመፀኛና የሚያስመርር ትውልድ፥ ልቡን ያላቀና ትውልድ፥ መንፈሱም በእግዚአብሔር ዘንድ ያልታመነ። የኤፍሬም ልጆች ለውጊያ ታጥቀው ቀስትንም ገትረው በጦርነት ቀን ወደ ኋላ ተመለሱ። የእግዚአብሔርን ኪዳን አልጠበቁም፥ በሕጉም ለመመላለስ እንቢ አሉ፥ መልካም ሥራውንና ያሳያቸውን ተኣምራቱን ረሱ፥ በግብጽ አገርና በጾዓን አገር በአባቶቻቸው ፊት የሠራውን ተኣምራት። ባሕርን ከፍሎ አሳለፋቸው፥ ውኆችን እንደ ግንብ አቆመ። ቀን በደመና መራቸው፥ ሌሊቱንም ሁሉ በእሳት ብርሃን። ዓለቱን በምድረ በዳ ሰነጠቀ፥ ከጥልቅ እንደሚገኝ ያህል በብዙ አጠጣቸው። ውኃን ከዓለት አወጣ፥ ውኃንም እንደ ወንዞች አፈሰሰ። ነገር ግን ይበድሉት ዘንድ እንደገና ደገሙ፥ ልዑልንም በምድረ በዳ አስቈጡት። የተመኙትን መብል እየጠየቁ፥ እግዚአብሔርን በልባቸው ፈተኑት። እግዚአብሔርን እንዲህ ብለው አሙት፦ “እግዚአብሔር በምድረ በዳ ማዕድን ያሰናዳ ዘንድ ይችላልን? ዓለቱን መታ፥ ውኆችም ወጡ፥ ወንዞችም ጐረፉ፥ እንጀራን መስጠትስ ይችላልን? ለሕዝቡስ ማዕድን ያዘጋጃልን?”