መጽሐፈ ምሳሌ 7:10-23

መጽሐፈ ምሳሌ 7:10-23 መቅካእኤ

እነሆ፥ ሴት ተገናኘችው የአምንዝራ ሴት ልብስ የለበሰች፥ ነፍሳትን ለማጥመድ የተዘጋጀች። ሁከተኛና እንቢተኛ ናት፥ እግሮችዋም በቤትዋ አይቀመጡም፥ አንድ ጊዜ በጎዳና፥ አንድ ጊዜ በአደባባይ፥ በማዕዘኑም ሁሉ ታደባለች። ያዘችውም ሳመችውም፥ ፊትዋም ያለ እፍረት ሆኖ እንዲህ አለችው፦ “መሥዋዕትንና የደኅንነት ቁርባንን ማቅረብ ነበረብኝ፥ ዛሬ ስእለቴን ፈጸምሁ። ስለዚህ እንድገናኝህ፥ ፊትህንም በትጋት ለመሻት ወጥቻለሁ፥ አግኝቼሃለሁም። በአልጋዬ ላይ ማለፊያ የአልጋ ልብስ ዘርግቼበታለሁ፥ የግብጽንም ያማሩ አልባሳት አንጥፌበታለሁ። በመኝታዬ ከርቤንና ዓልሙን ቀረፋም ረጭቼበታለሁ። ና፥ እስኪ ነጋ ድረስ በፍቅር እንርካ፥ በተወደደ መተቃቀፍም ደስ ይበለን። ባለቤቴ በቤቱ የለምና፥ ወደ ሩቅ መንገድ ሄዶአልና፥ በእጁም የብር ከረጢት ወስዶአል፥ ሙሉ ጨረቃ በሆነች ጊዜ ወደ ቤቱ ይመለሳል።” በብዙ ጨዋታዋ እንዲስት ታደርገዋለች፥ በከንፈርዋ ልዝብነት ትጐትተዋለች። እርሱ እንዲህ ስቶ ይከተላታል፥ በሬ ለመታረድ እንደሚነዳ፥ አጋዘን ቸኩሎ ወደ ወጥመድ እንደሚገባ፥ ወፍ ወደ ወጥመድ እንደሚጣደፍ፥ ለነፍሱ ጥፋት እንደሚሆን ሳያውቅ፥ ፍላጻ ጉበቱን እስኪሰነጥቀው ድረስ።