ዘኍልቍ 3:1-39

ዘኍልቍ 3:1-39 NASV

እግዚአብሔር ሙሴን በሲና ተራራ ላይ ባነጋገረው ጊዜ የአሮንና የሙሴ ትውልድ ይህ ነበር፤ የአሮን ልጆች የበኵሩ ስም ናዳብ፣ የሌሎቹም አብዩድ አልዓዛርና ኢታምር ይባላል። እርሱ ለክህነት አገልግሎት የለያቸው፣ ካህናት ለመሆን የተቀቡት የአሮን ወንድ ልጆች ስም ይህ ነው፤ ናዳብና አብዩድ ግን በሲና ምድረ በዳ ባልተፈቀደ እሳት ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ባቀረቡ ጊዜ እዚያው እፊቱ ወድቀው ሞቱ። ወንዶች ልጆች ስላልነበሯቸውም አልዓዛርና ኢታምር ብቻ አባታቸው አሮን በሕይወት በነበረበት ዘመን በክህነት ያገለግሉ ነበር። እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ አለው፤ “የሌዊን ነገድ አምጥተህ ካህኑን አሮንን በአገልግሎቱ እንዲረዱት ከፊቱ አቁማቸው፤ በመገናኛው ድንኳን የማደሪያውን አገልግሎት በመፈጸም ለርሱና ለማኅበረ ሰቡ ሁሉ የሚያስፈልጉትን ተግባሮች ያከናውኑ፤ የማደሪያውን ሥራ በመሥራትና የእስራኤላውያንን ግዴታ በመወጣት የመገናኛውን ድንኳን ሁሉ ይጠብቁ። ሌዋውያኑን ለአሮንና ለልጆቹ ስጥ፤ እነርሱም ከእስራኤላውያን ተለይተው ለርሱ ፈጽመው የተሰጡ ናቸው። አሮንንና ልጆቹን ሹማቸው፤ እነርሱም ክህነታቸውን ይጠብቁ፤ ሌላ ሰው ማደሪያውን ቢቀርብ ግን ይገደል።” እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ አለው፤ “እነሆ፤ በኵር ሆኖ በሚወለደው ሁሉ ምትክ ሌዋውያኑን ከእስራኤላውያን ወስጃለሁ፤ ስለዚህ ሌዋውያን የእኔ ናቸው፤ በኵር የሆነ ሁሉ የእኔ ነውና። በግብጽ ምድር በኵር የሆነውን ሁሉ በመታሁ ዕለት ከሰውም ሆነ ከእንስሳ ማንኛውንም የእስራኤልን በኵር ለራሴ ለይቻለሁ፤ የእኔ ይሁን። እኔ እግዚአብሔር ነኝ።” እግዚአብሔር ሙሴን በሲና ምድረ በዳ፣ “ሌዋውያንን በየቤታቸውና በየጐሣቸው ቍጠር፤ የምትቈጥረውም አንድ ወርና ከዚያ በላይ የሆነውን ወንድ ሁሉ ነው” አለው። ስለዚህ ሙሴ በእግዚአብሔር ቃል በታዘዘው መሠረት እነዚህን ቈጠራቸው። የሌዊ ልጆች ስም ጌርሶን፣ ቀዓትና ሜራሪ ነው። የጌርሶን ልጆች ጐሣ ስም ሎቤኒና ሰሜኢ ነው። የቀዓት ጐሣዎች፤ እንበረም፣ ይስዓር፣ ኬብሮን፣ ዑዝኤል። የሜራሪ ጐሣዎች፤ ሞሖሊና ሙሲ። እንግዲህ የሌዋውያን ጐሣዎች በየቤተ ሰባቸው ሲቈጠሩ እነዚህ ናቸው። የሊብናና የሰሜኢ ጐሣዎች ከጌርሶን ወገን ናቸው፤ እነዚህ የጌርሶን ጐሣዎች ነበሩ። አንድ ወርና ከዚያ በላይ ሆኗቸው የተቈጠሩት ወንዶች በሙሉ ብዛታቸው ሰባት ሺሕ ዐምስት መቶ ነበር። የጌርሶን ጐሣዎች በምዕራብ በኩል ከማደሪያው ድንኳን ጀርባ ይሰፍራሉ። የጌርሶን ጐሣዎች ቤተ ሰቦች አለቃ የዳኤል ልጅ ኤሊሳፍ ይሆናል። የጌርሶናውያን ኀላፊነት በመገናኛው ድንኳን ማደሪያውንና ድንኳኑን፣ መደረቢያዎቹን እንዲሁም በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ ያለውን መጋረጃ፣ የአደባባዩን መጋረጃዎች፣ ማደሪያ ድንኳኑንና መሠዊያውን የሚጋርደውን የአደባባዩን መግቢያ መጋረጃ፣ ገመዶቹንና ከነዚሁ ጋራ ተያይዞ አገልግሎት የሚሰጠውን ሁሉ መጠበቅ ይሆናል። የእንበረማውያን፣ የይስዓራውያን፣ የኬብሮናውያንና የዑዝኤላውያን ጐሣዎች ከቀዓት ወገን ናቸው፤ እነዚህ የቀዓት ጐሣዎች ነበሩ። አንድ ወርና ከዚያ በላይ ሆኗቸው የተቈጠሩት ወንዶች በሙሉ ብዛታቸው ስምንት ሺሕ ስድስት መቶ ሲሆን፣ ቀዓታውያንም መቅደሱን የመጠበቅ ኀላፊነት ነበራቸው። የቀዓት ጐሣዎች ከማደሪያው ድንኳን በደቡብ በኩል ይሰፍራሉ። የቀዓት ጐሣዎች ቤተ ሰቦች አለቃ የዑዝኤል ልጅ ኤሊጻፋን ይሆናል። እነርሱም ታቦቱን፣ ጠረጴዛውን፣ መቅረዙን፣ መሠዊያዎቹን፣ ለመቅደሱ አገልግሎት የሚውሉትን ዕቃዎች፣ መጋረጃዎችንና ከነዚህ ጋራ ተያይዞ አገልግሎት የሚሰጠውን ሁሉ ይጠብቃሉ። ዋናው የሌዋውያን አለቃ የካህኑ የአሮን ልጅ አልዓዛር ነው፤ እርሱም መቅደሱን ለመጠበቅ ኀላፊ በሆኑት ላይ ተሹሞ ነበር። የሞሖላውያንና የሙሳያውያን ጐሣዎች ከሜራሪ ወገን ናቸው፤ እነዚህም የሜራሪ ጐሣዎች ነበሩ። አንድ ወርና ከዚያ በላይ ሆኗቸው የተቈጠሩት ወንዶች ሁሉ ብዛታቸው ስድስት ሺሕ ሁለት መቶ ነበር። የሜራሪም ጐሣዎች ቤተ ሰቦች አለቃ የአቢካኢል ልጅ ሱሪኤል ይሆናል፤ የሜራሪም ጐሣዎች ከማደሪያው ድንኳን በሰሜን በኩል ይሰፍራሉ። ሜራሪያውያንም የማደሪያውን ድንኳን ሳንቃዎች፣ መወርወሪያዎች፣ ምሰሶዎች፣ ምሰሶዎቹ የሚቆሙባቸውን እግሮች፣ የማደሪያ ዕቃዎችን ሁሉና ከነዚሁ ጋራ ተያይዞ አገልግሎት የሚሰጠውን ሁሉ ለመጠበቅ ተሹመው ነበር። እንዲሁም የአደባባዩን ዙሪያ ምሰሶዎች ከነመቆሚያ እግሮቻቸው፣ ከነካስማቸውና ከነገመዶቻቸው ይጠብቃሉ። ሙሴ፣ አሮንና ልጆቹ ከማደሪያው ድንኳን በምሥራቅ በኩል በፀሓይ መውጫ ከመገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት ይሰፍራሉ። እነርሱም እስራኤላውያንን ወክለው ማደሪያ ድንኳኑን ለመጠበቅ ኀላፊዎች ይሆናሉ። ወደ ማደሪያው ድንኳን የሚቀርብ ማንኛውም ሌላ ሰው ግን ይገደል። አንድ ወርና ከዚያ በላይ ሆኗቸው፣ ሙሴና አሮን በእግዚአብሔር ትእዛዝ በየጐሣቸው የቈጠሯቸው የሌዋውያን ወንዶች ልጆች ጠቅላላ ብዛት ሃያ ሁለት ሺሕ ነበር።