ዘኍልቍ 12:1-13

ዘኍልቍ 12:1-13 NASV

ሙሴ ኢትዮጵያዊት ሴት አግብቶ ነበርና ባገባት ኢትዮጵያዊት ምክንያት ማርያምና አሮን ይነቅፉት ጀመር። እነርሱም፣ “ለመሆኑ እግዚአብሔር የተናገረው በሙሴ አማካይነት ብቻ ነውን? በእኛስ አልተናገረም?” ተባባሉ፤ እግዚአብሔርም ይህን ሰማ። ሙሴ በምድር ላይ ካሉት ሰዎች ሁሉ ይልቅ እጅግ ትሑት ሰው ነበር። ወዲያው እግዚአብሔር ሙሴን፣ አሮንንና ማርያምን፣ “ሦስታችሁም ውጡና ወደ መገናኛው ድንኳን ኑ” አላቸው፤ ሦስቱም ወጥተው ሄዱ። ከዚያም እግዚአብሔር በደመና ዐምድ ወረደ፤ በድንኳኑም ደጃፍ ቆሞ አሮንንና ማርያምን ጠራቸው፤ ሁለቱም ወደ እርሱ በቀረቡ ጊዜ፣ እንዲህ አላቸው፤ “ቃሌን ስሙ፤ “የእግዚአብሔር ነቢይ በመካከላችሁ ቢኖር፣ በራእይ እገለጥለታለሁ፤ በሕልምም እናገረዋለሁ። ለአገልጋዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም፤ እርሱ በቤቴ ሁሉ የታመነ ነው። እኔ ከርሱ ጋራ የምነጋገረው ፊት ለፊት ነው፤ በግልጽ እንጂ በልዩ ዘይቤ አይደለም፤ እርሱ የእግዚአብሔርን መልክ ያያል። ታዲያ እናንተ አገልጋዬን ሙሴን ትቃወሙ ዘንድ ለምን አልፈራችሁም?” የእግዚአብሔር ቍጣ በላያቸው ነደደ፤ እርሱም ትቷቸው ሄደ። ደመናው ከድንኳኑ ላይ በተነሣ ጊዜ፣ እነሆ፤ ማርያም በለምጽ ተመታች፤ እንደ በረዶም ነጣች። አሮንም ወደ እርሷ ዘወር ሲል ለምጽ ወርሷት አየ፤ ሙሴንም እንዲህ አለው፣ “ጌታዬ ሆይ፤ በስንፍናችን የሠራነውን ኀጢአት እባክህ አትቍጠርብን። እርሷንም በእናቱ ማሕፀን ሳለ ሞቶ ግማሽ አካሉ ከተበላ በኋላ የተወለደ ጭንጋፍ መስላ እንድትቀር አታድርግ።” ስለዚህም ሙሴ፣ “አምላክ ሆይ፤ እባክህ ፈውሳት” ብሎ ወደ እግዚአብሔር ጮኸ።