ሚክያስ 4:1-5

ሚክያስ 4:1-5 NASV

በመጨረሻው ዘመን፣ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ተራራ፣ ከተራሮችም ከፍ ብሎ ይመሠረታል፤ ከኰረብቶችም በላይ ከፍ ይላል፤ ሕዝቦችም ወደ እርሱ ይጐርፋሉ። ብዙ አሕዛብ መጥተው እንዲህ ይላሉ፤ “ኑ፤ ወደ እግዚአብሔር ተራራ፣ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤት እንውጣ፤ በጐዳናውም እንድንሄድ፣ መንገዱን ያስተምረናል።” ሕግ ከጽዮን፤ የእግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣልና። እርሱ በብዙ ሕዝብ መካከል ይፈርዳል፤ በሩቅና በቅርብ ባሉ ኀያላን መንግሥታት መካከል ያለውን ግጭት ያቆማል፤ ሰይፋቸውን ማረሻ፣ ጦራቸውንም ማጭድ ያደርጉታል። አንዱ መንግሥት በሌላው መንግሥት ላይ ሰይፍ አያነሣም፤ ከእንግዲህም የጦርነት ትምህርት አይማሩም። እያንዳንዱ ሰው በገዛ ወይኑ ሥር፣ ከገዛ በለሱም ሥር ይቀመጣል፤ የሚያስፈራቸው አይኖርም፤ የሰራዊት ጌታ የእግዚአብሔር አፍ ተናግሯልና። አሕዛብ ሁሉ፣ በአማልክታቸው ስም ይሄዳሉ፤ እኛ ግን በአምላካችን በእግዚአብሔር ስም፣ ከዘላለም እስከ ዘላለም እንሄዳለን።