ዕዝራ 7:1-10

ዕዝራ 7:1-10 NASV

ከእነዚህም ነገሮች በኋላ በፋርስ ንጉሥ በአርጤክስስ ዘመነ መንግሥት፣ ዕዝራ የሠራያ ልጅ፣ የዓዛርያስ ልጅ፣ የኬልቅያስ ልጅ የሰሎም ልጅ፣ የሳዶቅ ልጅ፣ የአኪጦብ ልጅ፣ የአማርያ ልጅ፣ የዓዛርያስ ልጅ፣ የመራዮት ልጅ፣ የዘራእያ ልጅ፣ የኦዚ ልጅ፣ የቡቂ ልጅ፣ የአቢሱ ልጅ፣ የፊንሐስ ልጅ፣ የአልዓዛር ልጅ፣ የታላቁ ካህን የአሮን ልጅ፤ ይህ ዕዝራ ከባቢሎን መጣ፤ እርሱም የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጠውን ሕግ በሚገባ የሚያውቅ የሕግ መምህር ነበር። የአምላኩ የእግዚአብሔር እጅ በርሱ ላይ ስለ ነበረች፣ የጠየቀውን ሁሉ ንጉሡ ፈቀደለት። እንደዚሁም አንዳንድ እስራኤላውያን፣ ከካህናት፣ ከሌዋውያን፣ ከመዘምራን፣ ከበር ጠባቂዎችና ከቤተ መቅደሱ አገልጋዮች ጋራ በመሆን በንጉሡ በአርጤክስስ ዘመነ መንግሥት በሰባተኛው ዓመት ወደ ኢየሩሳሌም መጡ። ዕዝራ በንጉሡ ሰባተኛ ዓመት በዐምስተኛው ወር ኢየሩሳሌም ደረሰ። መልካሚቱ የእግዚአብሔር እጅ በርሱ ላይ ስለ ነበረች፣ ከባቢሎን በመጀመሪያው ወር በመጀመሪያው ቀን ተነሥቶ በዐምስተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ኢየሩሳሌም ደረሰ። ዕዝራ የእግዚአብሔርን ሕግ በማጥናትና በማድረግ፣ ለእስራኤልም ሥርዐቱንና ሕጉን በማስተማር ራሱን ፈጽሞ ሰጥቶ ነበር።