ኦሪት ዘፍጥረት መግቢያ

መግቢያ
ኦሪት ዘፍጥረት ከኦሪት መጽሐፎች ቀዳሚው ነው። ኦሪት ዘፍጥረት የሚለው የአማርኛው ርእስና በሌሎች ቋንቋዎች ታትመው የምናገኛቸው ሥራዎች የሰባ ሊቃናቱን ስያሜ የተከተሉ ሲሆን፥ የግሪኩን 5፥1 “የአዳም የዘር ሐረግ መጽሐፍ ይህ ነው” ከሚለው ይነሣል። የዕብራይስጡ የርእስ አሰጣጥ ባህል የተለየ ነበር። የአንድ መጽሐፍ ወይም የብራና ጥቅል የመጀመሪያ ቃል ወይም ቃላት ተወስደው ለርእስነት ያገለግላሉ። በዚህም መሠረት ኦሪት ዘፍጥረት በዕብራይስጥ ባሕል “በሬሺት” ተብሎ ነው የሚጠራው። ቃል በቃል ፍቹ “በመጀመርያ” ማለት ነው።
ኦሪት ዘፍጥረት በሁለት ዋና ክፍሎች የተዋቀረ ነው። እነርሱም፦ ዘፍ. 1፥1—11፥26 እና 11፥27—50፥26 ናቸው። እነኚህ ሁለት ክፍሎች ትይዩ ናቸው። ዘፍ. 1፥11—11፥26 የትውልዶችን መነሻ ይገልጻል፤ እግዚአብሔር ዓለምን እንዴት እንደፈጠረ፥ ምድርንም በሰው ልጆች እንዴት እንደሞላት፥ ከሰው ልጆች ጋር ምን ዓይነት ቃል ኪዳን እንዳቆመ ይገልጻል። ዘፍ. 11፥27—50፥26 የእስራኤልን አባቶች ታሪክ ያቀርባል። ይህም እግዚአብሔር እንዴት አድርጎ እስራኤልን እንደጠራ ካሳየ በኋላ አምላክ የሰጣቸውን በረከትና ምድር እንዴት እንደሚወርሱ ያሳያል። በሁለተኛው ክፍል ውስጥ ታሪኮቹን የሚከፍሉ ሦስት ዋነኛ መለያዎች አሉ። እነርሱም፦ 1. አብርሃምና ሣራ (11፥27—25፥18)፤ 2. ያዕቆብና ልጆቹ (25፥19—36፥43)፤ እና 3. ዮሴፍና ወንድሞቹ (37፥1—50፥26) ናቸው።
ኦሪት ዘፍጥረት፥ እንደ ስያሜው ስለ ፍጥረት፥ ስለ ዓለምና ስለ ሕይወት፥ ስለ ሰው፥ ስለ ኃጢአት፥ እንደዚሁም ስለ ተመረጡ ሕዝቦች ጅማሬ ይገልጻል። ታሪኩ በአጠቃላይ እግዚአብሔር በራሱ የማዳን እቅድ የሰው ልጆችን ታሪክ ሲመራ፥ ለሰው ያለውን የፍቅሩን ጥበቃ ያሳያል። እንግዲህ የኦሪት ዘፍጥረት ትኩረትም እንደሚከተለው ነው፤ ስለ አዳም፥ በእግዚአብሔርና በፍጥረት መሀል ስለተደረገው ቃል ኪዳን፥ ስለ ኖህ፥ ስለ እስራኤል አባቶች ታሪክ፥ ማለትም ስለ አብርሃም፥ ስለ ይስሐቅ፥ ስለ ያዕቆብና ስለ ዮሴፍ ያስተምራል።
አጠቃላይ የመጽሐፉ ይዘት
ፍጥረት (1፥1—2፥25)
የኃጢአትና የችግር አጀማመር (3፥1-24)
ከአዳም እስከ ኖኅ (4፥1—5፥32)
ኖኅና የጥፋት ውሃ (6፥1—10፥32)
የባቢሎን ግንብ (11፥1-9)
ከሴም እስከ አብርሃም (11፥10-32)
አባቶች አብርሃም፥ ይስሐቅ፥ ያዕቆብ (12፥1—35፥29)
የኤሳው ትውልድ (36፥1-43)
ዮሴፍና ወንድሞቹ (37፥1—45፥28)
እስራኤላውያን በግብጽ (46፥1—50፥26)
ምዕራፍ

Marker

Del

Kopier

None

Vil du ha høydepunktene lagret på alle enhetene dine? Registrer deg eller logg på

YouVersion bruker informasjonskapsler for å tilpasse opplevelsen din. Ved å bruke nettstedet vårt godtar du vår bruk av informasjonskapsler, som beskrevet i vår Personvernerklæring