አሁን ግን፣ ያዕቆብ ሆይ የፈጠረህ፣
እስራኤል ሆይ! የሠራህ፣
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤
“ተቤዥቼሃለሁና አትፍራ፤
በስምህ ጠርቼሃለሁ፤ አንተ የእኔ ነህ፤
በውሃ ውስጥ በምታልፍበት ጊዜ፣
ከአንተ ጋራ እሆናለሁ፤
ወንዙን ስትሻገረው፣
አያሰጥምህም፤
በእሳት ውስጥ ስትሄድ፣
አያቃጥልህም፤
ነበልባሉም አይፈጅህም።
እኔ እግዚአብሔር አምላክህ፣
የእስራኤልም ቅዱስ መድኀኒትህ ነኝና፤
ግብጽን ለአንተ ቤዛ እንድትሆን፣
ኢትዮጵያንና ሳባን በአንተ ፈንታ እሰጣለሁ።