ሮሜ 7:4-6 - Compare All Versions
ሮሜ 7:4-6 አማ2000 (የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ))
ወንድሞች ሆይ! እናንተ እንዲሁ የክርስቶስ አካል ስለ ሆናችሁ ከኦሪት ተለይታችኋል፤ ለእግዚአብሔርም ፍሬ እንድታፈሩ ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው ለዳግማዊ አዳም ሆናችኋል። የሰውን ሕግ በሠራን ጊዜ ግን በኦሪት ሕግ ደካማነት ቅጣቱ ጸናብን፤ ሞትንም አፈራን። አሁን ግን ታስረንበት ከነበረው ከኦሪት ሕግ ነፃ ወጥተናል፤ ስለዚህ በብሉይ መጽሐፍ ሳይሆን በአዲሱ መንፈሳዊ ሕይወት እንገዛለን።
ሮሜ 7:4-6 NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
ስለዚህ ወንድሞቼ ሆይ፤ እናንተም በክርስቶስ ኢየሱስ ሥጋ ለሕግ ሞታችኋል፤ ይህም ከሙታን ለተነሣው ለርሱ፣ ለሌላው ሆናችሁ ለእግዚአብሔር ፍሬ እንድናፈራ ነው። ኀጢአተኛ በሆነ ተፈጥሮ ቍጥጥር ሥር ሳለን፣ ለሞት ፍሬ እንድናፈራ በሕግ የተቀሰቀሰው የኀጢአት መሻት በሥጋችን ላይ ይሠራ ነበር። አሁን ግን ቀድሞ ጠፍሮ አስሮን ለነበረው ሞተን፣ ከሕግ ነጻ ወጥተናል፤ ይህም አሮጌ በሆነው በተጻፈው ሕግ ሳይሆን፣ አዲስ በሆነው በመንፈስ መንገድ እንድናገለግል ነው።
ሮሜ 7:4-6 አማ54 (መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት))
እንዲሁ፥ ወንድሞቼ ሆይ፥ እናንተ ደግሞ በክርስቶስ ሥጋ ለሕግ ተገድላችኋል፤ ለእግዚአብሔር ፍሬ እንድናፈራ፥ እናንተ ለሌላው፥ ከሙታን ለተነሣው፥ ለእርሱ ትሆኑ ዘንድ። በሥጋ ሳለን በሕግ የሚሆን የኃጢአት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሠራ ነበርና፤ አሁን ግን ለእርሱ ለታሰርንበት ስለ ሞትን፥ ከሕግ ተፈትተናል፥ ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም።
ሮሜ 7:4-6 አማ05 (አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም)
ወንድሞቼ ሆይ፥ የእናንተም ሁኔታ እንደዚሁ ነው፤ እናንተ የክርስቶስ አካል ክፍል ስለ ሆናችሁ በሞት የመለየትን ያኽል ከሕግ ተለይታችኋል፤ ስለዚህ ለእግዚአብሔር አገልግሎት ፍሬ እንድናፈራ ከሞት የተነሣው የክርስቶስ ወገኖች ሆናችኋል። በሥጋ ፈቃድ እንመላለስ በነበረበት ጊዜ በሕግ የሚነሣሣው ክፉ ምኞት ለሞት ፍሬ እንድናፈራ በሰውነታችን ክፍሎች ውስጥ ይሠራ ነበር። አሁን ግን አስሮን ከነበረው ሕግ በሞት የመለየት ያኽል ስለ ተለየን ከሕግ እስራት ነጻ ወጥተናል፤ ስለዚህ ከእንግዲህ የምናገለግለው በአዲሱ መንፈሳዊ መመሪያ እንጂ አስቀድሞ በተጻፈው በአሮጌው የሕግ መመሪያ አይደለም።
ሮሜ 7:4-6 መቅካእኤ (መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ))
ስለዚህ ወንድሞቼ ሆይ! እናንተ ደግሞ በክርስቶስ ሥጋ ለሕግ ተገድላችኋል፤ እናንተ ለሌላው፥ ከሙታን ለተነሣው፥ ለእርሱ እንድትሆኑና ለእግዚአብሔር ፍሬ እንድናፈራ ነው። በሥጋ እያለን የኃጢአት ሥቃይ በሕግ በኩል ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በሰውነታችን ክፍሎች ይሠራ ነበር። አሁን ግን ለእርሱ ታስረን ከነበርንበት በመሞት ከሕግ ተፈትተናል፤ ስለዚህም በአሮጌው በፊደል ሳይሆን በአዲስ በመንፈስ ኑሮ እናገለግላለን።