መዝሙር 85:1-13
መዝሙር 85:1-13 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ) (አማ2000)
አቤቱ፥ ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል ስማኝም፥ ድሃና ምስኪን ነኝና። እኔ የዋህ ነኝና ነፍሴን ጠብቃት፤ አምላኬ ሆይ፥ አንተን የታመነውን ባሪያህን አድነው። አቤቱ፥ ቀኑን ሁሉ ወደ አንተ እጮኻለሁና ይቅር በለኝ። የባሪያህን ነፍስ ደስ አሰኛት፥ ነፍሴን ወደ አንተ አነሣለሁና። አቤቱ፥ አንተ መሓሪና ይቅር ባይ ነህና፥ ይቅርታህም ለሚጠሩህ ሁሉ ብዙ ነውና። አቤቱ፥ ጸሎቴን አድምጥ፥ የልመናዬንም ቃል ስማ። ትሰማኛለህና በመከራዬ ቀን ወደ አንተ እጮኻለሁ። አቤቱ፥ ከአማልክት የሚመስልህ የለም፥ እንደ ሥራህም ያለ የለም። የፈጠርሃቸው አሕዛብ ሁሉ ይምጡ፥ አቤቱ፥ በፊትህም ይስገዱ፥ ስምህንም ያክብሩ፤ አቤቱ፥ ድንቅን የምታደርግ አንተ ታላቅ ነህና፥ አንተም ብቻህን ታላቅ አምላክ ነህና፥ አቤቱ መንገድህን ምራኝ፥ በእውነትህም እሄዳለሁ፤ ስምህንም ለመፍራት ልቤን ደስ ይለዋል። አቤቱ፥ አምላኬ ሆይ፥ በልቤ ሁሉ አመሰግንሃለሁ። ለዘለዓለምም ስምህን አከብራለሁ፤ ምሕረትህ በእኔ ላይ ታላቅ ናትና፥ ነፍሴንም ከታችኛዪቱ ሲኦል አድነሃታልና።
መዝሙር 85:1-13 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
እግዚአብሔር ሆይ፤ ለምድርህ በጎ ውለሃል፤ የያዕቆብንም ምርኮ መለስህ። የሕዝብህን በደል ይቅር አልህ፤ ኀጢአታቸውንም ሁሉ ሸፈንህ። ሴላ መዓትህን ሁሉ አራቅህ፤ ከብርቱ ቍጣህም ተመለስህ። መድኀኒታችን የሆንህ አምላክ ሆይ፤ መልሰን፤ በእኛ ላይ የተቃጣውን ቍጣህን መልሰው። የምትቈጣን ለዘላለም ነውን? ቍጣህስ ከትውልድ እስከ ትውልድ ይቀጥላልን? ሕዝብህ በአንተ ሐሤት ያደርግ ዘንድ፣ መልሰህ ሕያዋን አታደርገንምን? እግዚአብሔር ሆይ፤ ምሕረትህን አሳየን፤ ማዳንህን ለግሰን። እግዚአብሔር አምላክ የሚናገረውን እሰማለሁ፤ ለሕዝቡ፣ ለቅዱሳኑ ሰላምን ይናገራልና፤ ዳሩ ግን ወደ ከንቱ ምግባራቸው አይመለሱ። ክብሩ በምድራችን ይኖር ዘንድ፣ ማዳኑ ለሚፈሩት በርግጥ ቅርብ ነው። ምሕረትና ታማኝነት ተገናኙ፤ ጽድቅና ሰላም ተቃቀፉ። ታማኝነት ከምድር በቀለች፤ ጽድቅም ከሰማይ ተመለከተች። እግዚአብሔር በጎ ነገር ይለግሳል፤ ምድራችንም ፍሬዋን ትሰጣለች። ጽድቅ በፊቱ ይሄዳል፤ ለአረማመዱም መንገድ ያዘጋጃል።
መዝሙር 85:1-13 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
እግዚአብሔር ሆይ! ለምድርህ ምሕረትን አሳየህ፤ የያዕቆብን ዘር እንደገና አበለጸግህ። የሕዝብህን በደል ይቅር አልክ፤ ኃጢአታቸውንም ሁሉ ደመሰስክ። እነርሱን ከመቈጣት ታገሥህ፤ ብርቱ ቊጣህንም መለስህ። አዳኛችን እግዚአብሔር ሆይ! ከተሰደድንበት መልሰን፤ በእኛም ላይ ያለህን ቅርታ አርቅልን። በእኛ ላይ የምትቈጣው ለዘለዓለም ነውን? ቊጣህንስ ከትውልድ ወደ ትውልድ ታስተላልፋለህን? እኛ ሕዝብህ በአንተ እንደሰት ዘንድ፥ እንደገና ሕይወትን አትዘራብንምን? እግዚአብሔር ሆይ! ዘለዓለማዊ ፍቅርህን አሳየን፤ አድነንም። እግዚአብሔር አምላክ የሚናገረውን ቃል ልስማ፤ እንደገና በስሕተት መንገድ ካልሄዱ በቀር፥ ለሕዝቡና ለታማኞቹ ሰላምን እንደሚሰጥ ተስፋ ሰጥቶአል። ክብሩ በምድራችን ይኖር ዘንድ፥ እርሱን ለሚፈሩት አዳኝነቱ ቅርብ ነው። ፍቅርና እውነት ይተቃቀፋሉ፤ ጽድቅና ሰላም ይስማማሉ። የሰው ታማኝነት ከምድር ይፈልቃል ጽድቅም ከሰማይ ወደ ታች ይመለከታል። እግዚአብሔር ያበለጽገናል፤ ምድራችንም ብዙ የመከር ፍሬ ትሰጠናለች። ፈለጉን እንከተል ዘንድ ጽድቅ በእግዚአብሔር ፊት ይሄዳል።
መዝሙር 85:1-13 መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) (መቅካእኤ)
አቤቱ፥ ምድርህን በመልካም ጎበኘህ፥ የያዕቆብንም ምርኮ መለስህ። የሕዝብህን በደል አስቀረህ፥ ኃጢአታቸውንም ሁሉ ይቅር አልክ። መዓትህንም ሁሉ አስወገድህ፥ ከቁጣህ መቅሠፍት ተመለስህ። የመድኃኒታችን አምላክ ሆይ፥ መልሰን፥ ቁጣህንም ከእኛ መልስ። በውኑ ለዘለዓለም ትቈጣናለህን? ቁጣህንስ ለልጅ ልጅ ታስረዝማለህን? አቤቱ፥ ሕይወትን ልትሰጠን አትመለስምን? ሕዝብም በአንተ ደስ ይላቸዋል። አቤቱ፥ ጽኑ ፍቅርህን አሳየን፥ አቤቱ፥ ማዳንህንም አሳየን። እግዚአብሔር የሚናገረውን እሰማለሁ፥ ወደ እብደታቸው ካልተመለሱ በቀር ጌታ ሰላምን ለሕዝቡና ለቅዱሳኑ ይናገራልና። ነገር ግን ክብር በምድራችን ያድር ዘንድ ማዳኑ ለሚፈሩት ቅርብ ነው። ጽኑ ፍቅርና እውነት ተገናኙ፥ ጽድቅና ሰላም ተቃቀፉ። እውነት ከምድር በቀለች፥ ጽድቅም ከሰማይ ተመለከተች። ጌታም በጎ ነገርን ይሰጣል፥ ምድራችንም ፍሬዋን ትሰጣለች።