ፊልጵስዩስ 3:10-15

ፊልጵስዩስ 3:10-15 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)

ሌላው ምክንያት ክርስቶስንና የክርስቶስን የትንሣኤ ኀይል ለማወቅ፥ የመከራው ተካፋይ ለመሆንና በሞቱም እርሱን ለመምሰል ነው። እንዲሁም ከሞትኩ በኋላ ተነሥቼ ለዘለዓለም በሕይወት ለመኖር ተስፋ በማድረግ ነው። ይህን ሁሉ ገና አላገኘሁም፤ ወይም በዚህ ሁሉ ፍጹም ሆኜአለሁ ለማለት አልችልም፤ ይሁን እንጂ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔን የእርሱ አድርጎ ያዘጋጀልኝን ሽልማት ለማግኘት ወደፊት በመሮጥ እተጋለሁ። ወንድሞቼ ሆይ! ገና ወደዚያ እንደ ደረስኩ አልቈጥርም፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ ይኸውም በስተኋላዬ የነበረውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እተጋለሁ። ሽልማቴንም ለማግኘት በፊቴ ወዳለው ግብ እሮጣለሁ፤ ይህም ሽልማት እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት ወደ ላይ ጠርቶ የሚሰጠኝ ሕይወት ነው። እንግዲህ በመንፈሳዊ ሕይወት የጠነከርን ሁሉ ይህን የመሰለ አስተሳሰብ ሊኖረን ይገባል፤ የምትለያዩበት ሐሳብ በመካከላችሁ ቢኖር ይህንንም ሐሳብ እግዚአብሔር ግልጥ ያደርግላችኋል።