ማቴዎስ 14:1-9
ማቴዎስ 14:1-9 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ) (አማ2000)
በዚያ ዘመን የአራተኛው ክፍል ገዥ ሄሮድስ የኢየሱስን ዝና ሰማ፤ ለሎሌዎቹም “ይህ መጥምቁ ዮሐንስ ነው፤ እርሱ ከሙታን ተነሥቶአል፤ ስለዚህም ኃይል በእርሱ ይደረጋል፤” አለ። ሄሮድስ በወንድሙ በፊልጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ዮሐንስን አስይዞ አሳስሮት በወህኒ አኑሮት ነበርና፤ ዮሐንስ “እርስዋ ለአንተ ትሆን ዘንድ አልተፈቀደም፤” ይለው ነበርና። ሊገድለውም ወዶ ሳለ፥ ሕዝቡ እንደ ነቢይ ስለ አዩት ፈራቸው። ነገር ግን ሄሮድስ የተወለደበት ቀን በሆነ ጊዜ፥ የሄሮድያዳ ልጅ በመካከላቸው ዘፈነች፤ ሄሮድስንም ደስ አሰኘችው፤ ስለዚህም የምትለምነውን ሁሉ እንዲሰጣት በመሐላ ተስፋ አደረገላት። እርስዋም በእናትዋ ተመክራ “የመጥምቁን የዮሐንስን ራስ በዚህ በወጭት ስጠኝ፤” አለችው። ንጉሡም አዘነ፤ ነገር ግን ስለ መሐላው ከእርሱም ጋር ተቀምጠው ስላሉት ሰዎች እንዲሰጡአት፤ አዘዘ፤
ማቴዎስ 14:1-9 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
በዚያ ጊዜ የአራተኛው ክፍል ገዥ የነበረው፣ ሄሮድስ ስለ ኢየሱስ ሰማ፤ ብላቴኖቹንም፣ “እንዲህ ከሆነ መጥምቁ ዮሐንስ ከሞት ተነሥቶ መጥቷል ማለት ነው፤ ይህ ሁሉ ድንቅ ታምራት በርሱ የሚደረገውም ለዚህ ነው” አላቸው። ቀደም ሲል ሄሮድስ፣ በወንድሙ በፊልጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ዮሐንስን አስይዞ ወህኒ አስገብቶት ነበር። ምክንያቱም ዮሐንስ፣ “እርሷን እንድታገባ ሕግ አይፈቅድልህም” ይለው ነበር። ሄሮድስም ዮሐንስን ሊገድለው ፈልጎ ነበር፤ ሕዝቡ ግን እንደ ነቢይ ይመለከተው ስለ ነበር ፈራ። ሄሮድስ የልደቱን ቀን ሲያከብር፣ የሄሮድያዳ ልጅ በዘፈን ደስ ስላሠኘችው፣ የምትጠይቀውን ሁሉ ሊሰጣት በመሐላ ቃል ገባላት። ልጅቷም በእናቷ ተመክራ፣ “የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ በሳሕን ላይ አድርገህ አሁኑኑ ስጠኝ” አለችው። በዚህ ጊዜ ንጉሡ ዐዘነ፤ ይሁን እንጂ ስለ መሐላውና ከርሱ ጋራ ስለ ነበሩ እንግዶች ሲል ጥያቄዋ እንዲፈጸምላት አዘዘ።
ማቴዎስ 14:1-9 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
በዚያ ዘመን የአራተኛው ክፍል ገዥ ሄሮድስ የኢየሱስን ዝና ሰማ፥ ለሎሌዎቹም፦ ይህ መጥምቁ ዮሐንስ ነው፤ እርሱ ከሙታን ተነሥቶአል፥ ስለዚህም ኃይል በእርሱ ይደረጋል አለ። ሄሮድስ በወንድሙ በፊልጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ዮሐንስን አስይዞ አሳስሮት በወህኒ አኑሮት ነበርና፤ ዮሐንስ፦ እርስዋ ለአንተ ትሆን ዘንድ አልተፈቀደም ይለው ነበርና። ሊገድለውም ወዶ ሳለ፥ ሕዝቡ እንደ ነቢይ ስለ አዩት ፈራቸው። ነገር ግን ሄሮድስ የተወለደበት ቀን በሆነ ጊዜ፥ የሄሮድያዳ ልጅ በመካከላቸው ዘፈነች ሄሮድስንም ደስ አሰኘችው፤ ስለዚህም የምትለምነውን ሁሉ እንዲሰጣት በመሐላ ተስፋ አደረገላት። እርስዋም በእናትዋ ተመክራ፦ የመጥምቁን የዮሐንስን ራስ በዚህ በወጭት ስጠኝ አለችው። ንጉሡም አዘነ፥ ነገር ግን ስለ መሐላው ከእርሱም ጋር ተቀምጠው ስላሉት ሰዎች እንዲሰጡአት አዘዘ፤
ማቴዎስ 14:1-9 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
በዚያን ጊዜ የገሊላ ክፍለ ሀገር ገዢ የነበረው ሄሮድስ፥ የኢየሱስን ዝና ሰማ። አገልጋዮቹን፥ “ይህ መጥምቁ ዮሐንስ ነው፤ እርሱ ከሞት ተነሥቶአል፤ እነዚህ ድንቅ ነገሮች በእርሱ አማካይነት የሚደረጉት ስለዚህ ነው” አላቸው። ሄሮድስ ዮሐንስን አስይዞ በወህኒ ቤት አሳስሮት ነበር፤ ይህንንም ያደረገው የወንድሙ የፊልጶስ ሚስት በነበረችው በሄሮዲያዳ ምክንያት ነው። ዮሐንስ ለሄሮድስ፦ “የወንድምህን ሚስት እንድታገባ ሕግ አይፈቅድልህም!” ብሎት ነበር። ስለዚህ ሄሮድስ ዮሐንስን ሊገድለው ይፈልግ ነበር፤ ነገር ግን የአይሁድ ሕዝብ እንደ ነቢይ ያዩት ስለ ነበር ሕዝቡን ፈራ። የሄሮድስ ልደት በሚከበርበት ቀን የሄሮድያዳ ልጅ መጥታ በተጋባዦች መካከል እየጨፈረች ሄሮድስን አስደሰተች። ስለዚህም ሄሮድስ፦ “የምትፈልጊውን ነገር ጠይቂኝ! እኔም እሰጥሻለሁ!” ሲል በመሐላ ቃል ገባላት። እርስዋም በእናቷ ተመክራ “የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ በሳሕን አሁኑኑ ስጠኝ!” አለችው። ንጉሡ በዚህ ነገር አዘነ፤ ይሁን እንጂ ስለ መሐላውና ከእርሱ ጋር በማእድ ተቀምጠው ስለ ነበሩት ሰዎች ይሉኝታ ብሎ የዮሐንስ ራስ እንዲሰጣት አዘዘ።
ማቴዎስ 14:1-9 መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) (መቅካእኤ)
በዚያ ዘመን የአራተኛው ክፍል ገዢ የነበረው ሄሮድስ የኢየሱስን ዝና ሰማ፤ አገልጋዮቹንም “ይህ መጥምቁ ዮሐንስ ነው፤ እርሱ ከሞት ተነሥቶአል፤ ኃይል በእርሱ የሚደረገውም ለዚህ ነው፤” አለ። ሄሮድስ በወንድሙ በፊልጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ዮሐንስን አስይዞ አሳስሮትና እስር ቤት አስገብቶት ነበርና፤ ዮሐንስ “እርሷ ለአንተ ትሆን ዘንድ ተገቢ አይደለም” ይለው ነበርና። ሊገድለው ይፈልግ ነበር፥ ነገር ግን ሕዝቡ እንደ ነቢይ ያዩት ስለ ነበር ፈራቸው። ነገር ግን ሄሮድስ የልደት ቀን በሆነ ጊዜ፥ የሄሮድያዳ ልጅ በመካከላቸው ጨፈረች፥ ሄሮድስንም ደስ አሰኘችው፤ የምትለምነውን ሁሉ እንደሚሰጣት በመሐላ ቃል ገባላት። እርሷም በእናትዋ ተመክራ “የመጥምቁን የዮሐንስን ራስ በዚህ ሳሕን አሁን ስጠኝ” አለችው። ንጉሡም አዘነ፤ ነገር ግን ስለ መሐላውና ከእርሱ ጋር ተቀምጠው ስለ ነበሩት ሰዎች ሲል እንዲሰጡአት አዘዘ፤