ማቴዎስ 12:22-28
ማቴዎስ 12:22-28 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ) (አማ2000)
ከዚህም በኋላ ጋኔን ያደረበትን ዕውር ድዳም ወደ እርሱ አመጡ፤ ዕውሩም ዲዳውም እስኪያይና እስኪናገር ድረስ ፈወሰው። ሕዝቡም ሁሉ ተገረሙና “እንጃ ይህ ሰው የዳዊት ልጅ ይሆንን?” አሉ። ፈሪሳውያን ግን ሰምተው “ይህ በብዔል ዜቡል በአጋንንት አለቃ ካልሆነ በቀር አጋንንትን አያወጣም፤” አሉ። ኢየሱስ ግን አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው “እርስ በርስዋ የምትለያይ መንግሥት ሁላ ትጠፋለች፤” እርስ በርሱ የሚለያይ ከተማም ሁሉ ወይም ቤት አይቆምም። ሰይጣንም ሰይጣንን የሚያወጣ ከሆነ፥ እርስ በርሱ ተለያየ፤ እንግዲህ መንግሥቱ እንዴት ትቆማለች? እኔስ በብዔል ዜቡል አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ ልጆቻችሁ በማን ያወጡአቸዋል? ስለዚህ እነርሱ ፈራጆች ይሆኑባችኋል። እኔ ግን በእግዚአብሔር መንፈስ አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ደርሳለች።
ማቴዎስ 12:22-28 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
ከዚህ በኋላ በጋኔን የተያዘ ዕውርና ድዳ የሆነ ሰው ወደ እርሱ አመጡ፤ ኢየሱስም ፈወሰው፤ ሰውየውም ማየትና መናገር ቻለ። ሕዝቡም ሁሉ ተደንቀው፣ “ይህ ሰው የዳዊት ልጅ ይሆንን?” አሉ። ነገር ግን ፈሪሳውያን ይህን በሰሙ ጊዜ፣ “ይህ ሰው አጋንንትን የሚያወጣው በአጋንንት አለቃ በብዔልዜቡል ብቻ መሆን አለበት” አሉ። ኢየሱስም ሐሳባቸውን ዐውቆ እንዲህ አላቸው፤ “እርስ በርሱ የሚከፋፈል መንግሥት ሁሉ ይወድቃል፤ እርስ በርሱም የተከፋፈለ ከተማ ወይም ቤት አይጸናም። ሰይጣንም ሰይጣንን የሚያስወጣ ከሆነ፣ እርስ በርሱ ተለያይቷል ማለት ነው፤ እንዲህ ከሆነ ደግሞ መንግሥቱ እንዴት ጸንቶ ሊቆም ይችላል? እኔ አጋንንትን የማስወጣው በብዔልዜቡል ከሆነ፣ ልጆቻችሁ በምን ሊያስወጧቸው ነው? ስለዚህ ልጆቻችሁ ይፈርዱባችኋል። እኔ ግን አጋንንትን የማስወጣው በእግዚአብሔር መንፈስ ከሆነ፣ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ መጥታለች።
ማቴዎስ 12:22-28 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
ከዚህም በኋላ ጋኔን ያደረበትን ዕውር ዲዳም ወደ እርሱ አመጡ፤ ዕውሩም ዲዳውም እስኪያይና እስኪናገር ድረስ ፈወሰው። ሕዝቡም ሁሉ ተገረሙና፦ እንጃ ይህ ሰው የዳዊት ልጅ ይሆንን? አሉ። ፈሪሳውያን ግን ሰምተው፦ ይህ በብዔል ዜቡል በአጋንንት አለቃ ካልሆነ በቀር አጋንንትን አያወጣም አሉ። ኢየሱስ ግን አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው፦ እርስ በርስዋ የምትለያይ መንግሥት ሁላ ትጠፋለች፥ እርስ በርሱ የሚለያይ ከተማም ሁሉ ወይም ቤት አይቆምም። ሰይጣንም ሰይጣንን የሚያወጣ ከሆነ፥ እርስ በርሱ ተለያየ፥ እንግዲህ መንግሥቱ እንዴት ትቆማለች? እኔስ በብዔል ዜቡል አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ ልጆቻችሁ በማን ያወጡአቸዋል? ስለዚህ እነርሱ ፈራጆች ይሆኑባችኋል። እኔ ግን በእግዚአብሔር መንፈስ አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ደርሳለች።
ማቴዎስ 12:22-28 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
ከዚህ በኋላ ሰዎች አንድ ጋኔን ያደረበትን ዕውርና ድዳ ሰው ወደ ኢየሱስ አመጡ፤ እርሱም ፈወሰው፤ ሰውየውም መናገርና ማየት ቻለ። ሕዝቡም ሁሉ ተገርመው፥ “ይህ የዳዊት ልጅ ይሆንን?” አሉ። ፈሪሳውያን ግን ይህን በሰሙ ጊዜ “እርሱ ‘ብዔልዜቡል’ በተባለው በአጋንንት አለቃ አማካይነት ካልሆነ በቀር አጋንንትን አያወጣም” አሉ። ኢየሱስም ሐሳባቸውን ዐውቆ እንዲህ አላቸው፦ “አንድ መንግሥት ተከፋፍሎ እርስ በእርሱ የሚጋጭ ከሆነ፥ ያ መንግሥት ይወድቃል። እንዲሁም አንድ ከተማ ወይም አንድ ቤተሰብ እርስ በርሱ ከተለያየ ጸንቶ መኖር አይችልም። ሰይጣንም ሰይጣንን የሚያስወጣ ከሆነ እርስ በርሱ ተለያየ ማለት ነው፤ ታዲያ፥ መንግሥቱ እንዴት ጸንቶ ሊኖር ይችላል! ደግሞ እኔ አጋንንትን የማስወጣቸው በብዔልዜቡል ከሆነ፥ ልጆቻችሁስ በምን ያስወጡአቸዋል? ስለዚህ ልጆቻችሁ በእናንተ ላይ ይፈርዱባችኋል። እኔ አጋንንትን የማስወጣ በእግዚአብሔር መንፈስ ከሆነ ግን እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት በእናንተ ላይ መጥታለች ማለት ነው።
ማቴዎስ 12:22-28 መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) (መቅካእኤ)
ከዚህ በኋላ ጋኔን ያደረበትን ዕውርና ዲዳ ወደ እርሱ አመጡ፤ እርሱም ፈወሰው፤ ዲዳውም ተናገረ አየም። ሕዝቡም ሁሉ ተገርመው “ይህ ሰው የዳዊት ልጅ ይሆንን?” አሉ። ፈሪሳውያን ግን ይህን ሰምተው “ይህ በአጋንንት አለቃ በብዔልዜቡል ካልሆነ በስተቀር አጋንንትን አያወጣም” አሉ። እርሱ ግን ሐሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው “እርስ በርስዋ የምትከፋፈል መንግሥት ሁላ ትጠፋለች፤ እርስ በርስዋ የምትከፋፈል ከተማ ወይም ቤት ሁላ አትቆምም። ሰይጣንም ሰይጣንን የሚያስወጣ ከሆነ፥ እርስ በርሱ ተለያየ ማለት ነው፤ እንግዲህ መንግሥቱ እንዴት መቆም ይችላል? እኔ አጋንንትን በብዔልዜቡል የማስወጣ ከሆነ፥ ልጆቻችሁ በማን ያስወጡአቸዋል? በዚህም ምክንያት እነርሱ ፈራጆች ይሆኑባችኋል። እኔ ግን በእግዚአብሔር መንፈስ አጋንንትን የማስወጣ ከሆንሁ፥ እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ መጥታለች።