አስቴር 1:19-22
አስቴር 1:19-22 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
“ስለዚህ ነገሩ ንጉሡን ደስ የሚያሠኘው ከሆነ፣ አስጢን ወደ ንጉሡ ወደ ጠረክሲስ ዘንድ ከእንግዲህ ወዲህ ፈጽሞ እንዳትገባ ንጉሣዊ ዐዋጅ ይውጣ፤ ይህም የማይሻር ሆኖ በፋርስና በሜዶን ሕጎች ይጻፍ፤ እንዲሁም ንጉሡ የእቴጌነቷን ክብር ከርሷ ለምትሻል ለሌላዪቱ ይስጥ። ከዚያም የንጉሡ ዐዋጅ በሰፊው ግዛቱ ሁሉ ሲነገር፣ ከትንሽ እስከ ትልቅ ያሉት ሴቶች ሁሉ ባሎቻቸውን ያከብራሉ።” ንጉሡና መኳንንቱ ሁሉ በዚህ ምክር ተደሰቱ፤ ንጉሡም ምሙካ ያቀረበውን ሐሳብ በሥራ ላይ አዋለው። እያንዳንዱ ሰው በራሱ ቤተ ሰብ ላይ ገዥ እንዲሆን መልእክት አስተላለፈ፤ መልእክቱም ለየአውራጃዎቹ በየራሳቸው ጽሑፍና ለእያንዳንዱ ሕዝብ በየራሱ ቋንቋ ተጽፎ በግዛቱ ሁሉ ተበተነ።
አስቴር 1:19-22 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
ንጉሡም ቢፈቅድ፥ አስጢን ወደ ንጉሡ ወደ አርጤክስስ ፊት ከእንግዲህ ወዲህ እንዳትገባ የንጉሡ ትእዛዝ ከእርሱ ይውጣ፥ እንዳይፈርስም በፋርስና በሜዶን ሕግ ይጻፍ፥ ንጉሡም ንግሥትነትዋን ከእርስዋ ለተሻለችው ለሌላይቱ ይስጥ። የንጉሡም ትእዛዝ በሰፊው መንግሥቱ ሁሉ በተነገረ ጊዜ ሴቶች ሁሉ ባሎቻቸውን ታላቁንም ታናሹንም ያከብራሉ። ይህም ምክር ንጉሡንና አዛውንቱን ደስ አሰኛቸው፥ ንጉሡም እንደ ምሙካን ቃል አደረገ። ሰው ሁሉ በቤቱ አለቃ ይሁን፥ በሕዝቡም ቋንቋ ይናገር ብሎ ለአገሩ ሁሉ እንደ ጽሕፈቱ ለሕዝቡም ሁሉ እንደ ቋንቋው ደብዳቤዎችን ወደ ንጉሡ አገሮች ሁሉ ሰደደ።
አስቴር 1:19-22 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
ንጉሥ ሆይ! እንግዲህ መልካም ፈቃድህ ቢሆን፥ ንግሥት አስጢን ከእንግዲህ ወዲህ ወደ አንተ ፊት መቅረብ ከቶ እንዳይፈቀድላት የሚገልጥ ውሳኔህን በዐዋጅ አስተላልፍ፤ ይህም ውሳኔ ከቶ የማይለወጥ ሆኖ ለዘለዓለም ይጸና ዘንድ በፋርስና በሜዶን ሕግ ውስጥ እንዲመዘገብ ትእዛዝ አስተላልፍ፤ የአስጢንንም የንግሥትነት ማዕርግ ከእርስዋ ለተሻለች ለሌላ ሴት ስጥ። አንተ የምታስተላልፈውም ዐዋጅ እጅግ ታላቅ በሆነው በዚህ በንጉሠ ነገሥት መንግሥትህ ግዛት ሁሉ በይፋ በሚነገርበት ጊዜ እያንዳንድዋ ሴት ባለጸጋም ይሁን ወይም ድኻ ባልዋን በአክብሮት ትመለከታለች።” ንጉሡና ባለሟሎቹ የሆኑ ባለሥልጣኖች ሁሉ ይህን ሐሳብ በደስታ ተቀበሉት፤ ንጉሡም መሙካን ያቀረበውን ምክር በሥራ ላይ አዋለ። ስለዚህም ንጉሡ “እያንዳንዱ ባል የቤቱ አባወራ ሆኖ በአዛዥነት የመናገር መብቱ የተጠበቀ ይሁን!” የሚል ትእዛዝ በየቋንቋውና በየአጻጻፍ ሥርዓቱ ተዘጋጅቶ ወደያንዳንዱ አገር እንዲተላለፍ አደረገ።