ሐዋርያት ሥራ 18:1-28 - Compare All Versions

ሐዋርያት ሥራ 18:1-28 አማ2000 (የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ))

ከዚህ በኋላ ጳው​ሎስ ከአ​ቴና ወጥቶ ወደ ቆሮ​ን​ቶስ ሄደ። አቂላ የሚ​ባል አንድ አይ​ሁ​ዳ​ዊም አገኘ፤ የት​ው​ልድ ሀገ​ሩም ጳን​ጦስ ነው፤ እር​ሱም ከጥ​ቂት ወራት በፊት ከኢ​ጣ​ልያ ተሰዶ መጣ፤ ሚስቱ ጵር​ስ​ቅ​ላም አብ​ራው ነበ​ረች፤ ቀላ​ው​ዴ​ዎስ አይ​ሁድ ከሮም እን​ዲ​ሰ​ደዱ አዝዞ ነበ​ርና ወደ እነ​ርሱ መጣ። ሥራ​ቸው አንድ ስለ ነበረ ድን​ኳን ሰፊ​ዎ​ችም ስለ ነበሩ ከእ​ነ​ርሱ ጋር አብሮ ኖረ፤ በአ​ን​ድ​ነ​ትም ይሠሩ ነበር። ጳው​ሎ​ስም በየ​ሰ​ን​በቱ በም​ኵ​ራብ ይከ​ራ​ከ​ራ​ቸው ነበር፤ አይ​ሁ​ድ​ንና አረ​ማ​ው​ያ​ን​ንም ያሳ​ም​ና​ቸው ነበር። ሲላ​ስና ጢሞ​ቴ​ዎ​ስም ከመ​ቄ​ዶ​ንያ በወ​ረዱ ጊዜ ጳው​ሎስ፥ ኢየ​ሱስ እርሱ ክር​ስ​ቶስ እንደ ሆነ ለአ​ይ​ሁድ እየ​መ​ሰ​ከረ ቃሉን በማ​ስ​ተ​ማር ይተጋ ነበር። እነ​ር​ሱም በተ​ቃ​ወ​ሙ​ትና በሰ​ደ​ቡት ጊዜ ልብ​ሱን አራ​ግፎ፥ “እን​ግ​ዲህ እኔ ንጹሕ ነኝ፤ ደማ​ችሁ በራ​ሳ​ችሁ ላይ ነው፤ ከእ​ን​ግ​ዲ​ህስ ወዲህ ወደ አሕ​ዛብ እሄ​ዳ​ለሁ” አላ​ቸው። ከዚ​ያም አልፎ ስሙ ኢዮ​ስ​ጦስ ወደ​ሚ​ባል እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን ወደ​ሚ​ፈራ ሰው ቤት ገባ፤ ቤቱም በም​ኵ​ራብ አጠ​ገብ ነበር። የም​ኵ​ራብ አለቃ ቀር​ስ​ጶ​ስም ከነ​ቤተ ሰቡ በጌ​ታ​ችን በኢ​የ​ሱስ ክር​ስ​ቶስ አመነ፤ ከቆ​ሮ​ን​ቶስ ሰዎ​ችም ብዙ​ዎች ሰም​ተው አም​ነው ተጠ​መቁ። ጌታ​ች​ንም ጳው​ሎ​ስን በሌ​ሊት ራእይ እን​ዲህ አለው፥ “አት​ፍራ፥ ነገር ግን ተና​ገር፥ ዝምም አት​በል፤ እኔ ከአ​ንተ ጋር ነኝና ማንም ሊጐ​ዳህ የሚ​ነ​ሣ​ብህ የለም፤ በዚች ከተማ ብዙ ሕዝብ አሉ​ኝና።” ጳው​ሎ​ስም የእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን ቃል እየ​አ​ስ​ተ​ማ​ራ​ቸው ዓመት ከስ​ድ​ስት ወር በቆ​ሮ​ን​ቶስ ተቀ​መጠ። ጋል​ዮ​ስም የአ​ካ​ይያ አገረ ገዢ በሆነ ጊዜ አይ​ሁድ ተባ​ብ​ረው በጳ​ው​ሎስ ላይ ተነሡ፤ ወደ ሸን​ጎም አመ​ጡት። እን​ዲ​ህም አሉት፥ “ይህ ሰው ኦሪ​ትን በመ​ቃ​ወም እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን ያመ​ልኩ ዘንድ ሰዎ​ችን ያባ​ብ​ላል።” ጳው​ሎ​ስም ይመ​ል​ስ​ላ​ቸው ዘንድ አፉን ሊከ​ፍት ወድዶ ሳለ አገረ ገዢው ጋል​ዮስ መልሶ አይ​ሁ​ድን እን​ዲህ አላ​ቸው፥ “እና​ንተ አይ​ሁድ ሆይ፥ የበ​ደ​ላ​ችሁ በደል ቢኖር፥ ወይም ሌላ በደል ቢኖ​ር​በት አቤ​ቱ​ታ​ች​ሁን በሰ​ማ​ሁና ባከ​ራ​ከ​ር​ኋ​ችሁ ነበር። ስለ ትም​ህ​ር​ትና ስለ ስሞች፥ ስለ ሕጋ​ች​ሁም የም​ት​ከ​ራ​ከሩ ከሆነ ግን ለራ​ሳ​ችሁ ዕወቁ፤ እኔ እን​ዲህ ያለ ነገር ልሰማ አል​ፈ​ቅ​ድም።” ከሸ​ን​ጎ​ውም አባ​ረ​ራ​ቸው። አረ​ማ​ው​ያ​ንም ሁሉ የም​ኵ​ራ​ቡን አለቃ ሶስ​ቴ​ን​ስን ይዘው በሸ​ንጎ ፊት ደበ​ደ​ቡት፤ የእ​ር​ሱም ነገር ጋል​ዮ​ስን ምንም አላ​ሳ​ዘ​ነ​ውም። ጳው​ሎ​ስም እንደ ገና በወ​ን​ድ​ሞቹ ዘንድ ጥቂት ቀን ተቀ​መጠ፤ በሰ​ላ​ምም ሸኙ​ትና ወደ ሶርያ በባ​ሕር ተጓዘ፤ ጵር​ስ​ቅ​ላና አቂ​ላም አብ​ረ​ውት ነበሩ፤ ስእ​ለ​ትም ነበ​ረ​በ​ትና በክ​ን​ክ​ራ​ኦስ ራሱን ተላጨ። ወደ ኤፌ​ሶ​ንም ደረሱ፤ በዚ​ያም ተዋ​ቸ​ውና እርሱ ብቻ​ውን ወደ ምኵ​ራብ ገብቶ አይ​ሁ​ድን ተከ​ራ​ከ​ራ​ቸው። እነ​ር​ሱም ብዙ ጊዜ እን​ዲ​ሰ​ነ​ብት ማለ​ዱት፤ ነገር ግን አል​ወ​ደ​ደም። ከዚ​ህም በኋላ በሚ​ሸ​ኙት ጊዜ፥ “እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ቢፈ​ቅድ እን​ደ​ገና እመ​ለ​ሳ​ለሁ፤ አሁን ግን የሚ​መ​ጣ​ውን በዓል በኢ​የ​ሩ​ሳ​ሌም ላደ​ርግ እወ​ዳ​ለሁ” አላ​ቸው፤ ከኤ​ፌ​ሶ​ንም በመ​ር​ከብ ሄደ። ወደ ቂሳ​ር​ያም ደረሰ፤ ከዚ​ያም ወጥቶ ለቤተ ክር​ስ​ቲ​ያን ሰላ​ምታ ከሰጠ በኋላ ወደ አን​ጾ​ኪያ ሄደ። ጥቂት ቀንም ተቀ​መጠ፤ ከዚ​ያም ወጥቶ በገ​ላ​ት​ያና በፍ​ር​ግያ በኩል በተራ እየ​ዞረ ሄደ፤ ደቀ መዛ​ሙ​ር​ት​ንም አጸ​ና​ቸው። በእ​ስ​ክ​ን​ድ​ር​ያም የሚ​ኖር፥ ንግ​ግር የሚ​ች​ልና መጽ​ሐ​ፍን የሚ​ያ​ውቅ አጵ​ሎስ የሚ​ባል አንድ አይ​ሁ​ዳዊ ሰው ወደ ኤፌ​ሶን መጣ። እር​ሱም የእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን መን​ገድ የተ​ማረ ነበር፤ ስለ ኢየ​ሱስ ክር​ስ​ቶ​ስም ሊያ​ስ​ተ​ም​ርና ሊመ​ሰ​ክር ከልቡ የሚ​ተጋ ነበር፤ ነገር ግን የዮ​ሐ​ን​ስን ጥም​ቀት ብቻ ተጠ​ምቆ ነበር። እር​ሱም በም​ኵ​ራብ በግ​ልጥ ይና​ገር ጀመር፤ ጵር​ስ​ቅ​ላና አቂ​ላም በሰ​ሙት ጊዜ ወደ ማደ​ሪ​ያ​ቸው ወስ​ደው ፍጹም የእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን መን​ገድ አስ​ረ​ዱት። ወደ አካ​ይ​ያም ሊሄድ በወ​ደደ ጊዜ ወን​ድ​ሞች አጽ​ና​ኑት፤ እን​ዲ​ቀ​በ​ሉ​ትም ወደ ደቀ መዛ​ሙ​ርት ጻፉ​ለት፤ ወደ እነ​ር​ሱም በደ​ረሰ ጊዜ፥ በእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ጸጋ ላመ​ኑት ብዙ አስ​ተ​ማ​ራ​ቸው፤ ትልቅ ርዳ​ታም ረዳ​ቸው። ተሰ​ብ​ስ​በው ሳሉም በሕ​ዝቡ ሁሉ ፊት አይ​ሁ​ድን በግ​ልጥ እጅግ ይከ​ራ​ከ​ራ​ቸው ነበር፤ ስለ ኢየ​ሱ​ስም እርሱ ክር​ስ​ቶስ እንደ ሆነ ከመ​ጻ​ሕ​ፍት ማስ​ረጃ ያመ​ጣ​ላ​ቸው ነበር።

ሐዋርያት ሥራ 18:1-28 NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)

ከዚህ በኋላ ጳውሎስ ከአቴና ተነሥቶ ወደ ቆሮንቶስ ሄደ። በዚያም የጳንጦስ ተወላጅ የሆነውን፣ አቂላ የተባለውን አይሁዳዊ አገኘ፤ እርሱም አይሁድ ሁሉ ከሮም እንዲወጡ ቀላውዴዎስ ባዘዘው መሠረት፣ ከሚስቱ ከጵርስቅላ ጋራ በቅርብ ጊዜ ከኢጣሊያ የመጣ ነበር። ጳውሎስም ሊያያቸው ወደ እነርሱ ሄደ፤ እርሱም እንደ እነርሱ ድንኳን ሰፊ ስለ ነበረ፣ ከእነርሱ ጋራ ተቀምጦ በተመሳሳይ ሥራ ላይ ተሰማራ። በየሰንበቱም ከአይሁድና ከግሪክ ሰዎች ጋራ በምኵራብ ውስጥ እየተነጋገረ ሊያሳምናቸው ይጥር ነበር። ሲላስና ጢሞቴዎስ ከመቄዶንያ በወረዱ ጊዜ፣ ጳውሎስ በስብከት እየተጋ፣ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደ ሆነ ለአይሁድ ይመሰክር ነበር። ነገር ግን በተቃወሙትና በሰደቡት ጊዜ ልብሱን አራግፎ፣ “ደማችሁ በራሳችሁ ላይ ይሁን! እኔ ንጹሕ ነኝ፤ ከእንግዲህ ወደ አሕዛብ እሄዳለሁ” አላቸው። ከዚያም ወጥቶ ቲቶስ ኢዮስጦስ ወደ ተባለ፣ እግዚአብሔርን ወደሚያመልክ ሰው ቤት ሄደ፤ የዚህም ሰው ቤት በምኵራቡ አጠገብ ነበር። የምኵራብ አለቃ የነበረው ቀርስጶስ ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋራ በጌታ አመነ፤ ጳውሎስ ሲናገር የሰሙ ብዙ የቆሮንቶስ ሰዎችም አምነው ተጠመቁ። ጌታም ሌሊት በራእይ ጳውሎስን እንዲህ አለው፤ “አትፍራ፤ ተናገር፣ ዝምም አትበል፤ እኔ ከአንተ ጋራ ነኝና ማንም በአንተ ላይ ተነሥቶ ሊጐዳህ አይችልም፤ በዚህች ከተማ ብዙ ሰዎች አሉኝና።” ስለዚህ ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ቃል እያስተማራቸው አንድ ዓመት ተኩል ዐብሯቸው ተቀመጠ። ጋልዮስ የአካይያ ገዥ በነበረበት ጊዜ አይሁድ ተባብረው በጳውሎስ ላይ ተነሡ፤ በፍርድ ወንበር ፊት አቅርበውትም፣ “ይህ ሰው ሕጉ በማይፈቅደው መንገድ፣ ሰዎች እግዚአብሔርን እንዲያመልኩ እያሳሳታቸው ነው” አሉ። ጳውሎስ ሊናገር ገና አፉን ሲከፍት፣ ጋልዮስ አይሁድን እንዲህ አላቸው፤ “የአይሁድ ሰዎች ሆይ፤ ያቀረባችሁት ጕዳይ ስለ ዐመፅ ወይም ስለ ከባድ ወንጀል ቢሆን ኖሮ ላደምጣችሁ በተገባኝ ነበር፤ ነገር ግን ክርክራችሁ ስለ ቃላትና ስለ ስሞች እንዲሁም ስለ ሕጋችሁ በመሆኑ፣ እናንተው ጨርሱት፤ እኔ በእንዲህ ዐይነት ነገር ፈራጅ ለመሆን አልሻም።” ስለዚህ ከፍርድ ወንበር ፊት አስወጣቸው። በዚህ ጊዜ ሁሉም የምኵራቡን አለቃ፣ ሶስቴንስን ይዘው በፍርድ ቤቱ ፊት ደበደቡት፤ ጋልዮስ ግን ነገሩ ደንታም አልሰጠውም። ከዚህ በኋላ ጳውሎስ ብዙ ቀን በቆሮንቶስ ተቀመጠ፤ ከዚያም ወንድሞችን ተሰናብቶ ከጵርስቅላና ከአቂላ ጋራ በመርከብ ወደ ሶርያ ሄደ። ስእለትም ስለ ነበረበት ክንክራኦስ በተባለ ቦታ ራሱን ተላጨ። ኤፌሶን በደረሰ ጊዜም ጵርስቅላንና አቂላን እዚያው ተዋቸው፤ እርሱ ራሱ ግን ወደ ምኵራብ ገብቶ ከአይሁድ ጋራ ይነጋገር ነበር። ከእነርሱ ጋራ እንዲሰነብት በጠየቁትም ጊዜ ፈቃደኛ አልሆነም፤ ነገር ግን ሲለያቸው፣ “የእግዚአብሔር ፈቃድ ከሆነ ተመልሼ እመጣለሁ” አላቸው፤ ከኤፌሶንም ተነሥቶ በመርከብ ተጓዘ። ቂሳርያም በደረሰ ጊዜ፣ ወጥቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምታ አቀረበ፤ ከዚያም ወደ አንጾኪያ ወረደ። በአንጾኪያም ጥቂት ጊዜ ከቈየ በኋላ፣ ከዚያ ተነሥቶ በገላትያና በፍርግያ አገሮች ከቦታ ቦታ በመዘዋወር ደቀ መዛሙርትን ሁሉ አበረታታ። በዚህ ጊዜ የእስክንድርያ ተወላጅ የሆነ አጵሎስ የሚባል አንድ አይሁዳዊ ወደ ኤፌሶን መጣ፤ እርሱም የተማረና ቅዱሳት መጻሕፍትን ጠንቅቆ የሚያውቅ ሰው ነበር። ይህ ሰው፣ የጌታን መንገድ የተማረ፣ ስለ ኢየሱስም በትክክል የሚናገርና በመንፈስ እየተቃጠለ የሚያስተምር ነበር፤ ይሁን እንጂ እርሱ የሚያውቀው የዮሐንስን ጥምቀት ብቻ ነበር። እርሱም በምኵራብ በድፍረት ይናገር ጀመር፤ ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜ፣ ወደ ቤታቸው ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ይበልጥ አስተካክለው አስረዱት። አጵሎስ ወደ አካይያ ለመሄድ በፈለገ ጊዜ፣ ወንድሞች አበረታቱት፤ በዚያ የነበሩት ደቀ መዛሙርትም እንዲቀበሉት ደብዳቤ ጻፉለት። እዚያም በደረሰ ጊዜ ከጸጋው የተነሣ አምነው ለነበሩት ትልቅ ረዳት ሆናቸው፤ ከቅዱሳት መጻሕፍት እያመሳከረ፣ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደ ሆነ ከአይሁድ ጋራ በጽኑ በመከራከር በሕዝብ ፊት ይረታቸው ነበርና።

ሐዋርያት ሥራ 18:1-28 አማ54 (መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት))

ከዚህም በኋላ ጳውሎስ ከአቴና ወጥቶ ወደ ቆሮንቶስ መጣ። በወገኑም የጳንጦስ ሰው የሚሆን አቂላ የሚሉትን አንድ አይሁዳዊ አገኘ፤ እርሱም ከጥቂት ጊዜ በፊት ከሚስቱ ከጵርስቅላ ጋር ከኢጣልያ መጥቶ ነበር፥ አይሁድ ከሮሜ ይወጡ ዘንድ ቀላውዴዎስ አዞ ነበርና፤ ወደ እነርሱ ቀረበ፥ ሥራቸውም አንድ ስለ ነበረ በእነርሱ ዘንድ ተቀምጦ በአንድ ላይ ሠሩ፤ ሥራቸው ድንኳን መስፋት ነበረና። በየሰንበቱም ሁሉ በምኵራብ ይነጋገር ነበር፥ አይሁድንና የግሪክንም ሰዎች ያስረዳ ነበር። ሲላስና ጢሞቴዎስም ከመቄዶንያ በወረዱ ጊዜ፥ ጳውሎስ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደ ሆነ ለአይሁድ እየመሰከረ ለቃሉ ይተጋ ነበር። ነገር ግን በተቃወሙትና በተሳደቡ ጊዜ፥ ልብሱን እያራገፈ፦ ደማችሁ በራሳችሁ ነው፤ እኔ ንጹሕ ነኝ ከእንግዲህ ወዲህ ወደ አሕዛብ እሄዳለሁ አላቸው። ከዚያም ወጥቶ ኢዮስጦስ ወደሚባል እግዚአብሔርን ወደሚያመልክ ሰው ቤት ገባ ቤቱም በምኩራብ አጠገብ ነበረ። የምኵራብ አለቃ ቀርስጶስም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር በጌታ አመነ፥ ከቆሮንቶስ ሰዎችም ብዙ በሰሙ ጊዜ አምነው ተጠመቁ። ጌታም ሌሊት በራእይ ጳውሎስን፦ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፥ ማንም ክፉ ሊያደርግብህ የሚነሣብህ የለምና አትፍራ፥ ነገር ግን ተናገር ዝምም አትበል፤ በዚህ ከተማ ብዙ ሕዝብ አሉኝና አለው። በመካከላቸውም የእግዚአብሔርን ቃል እያስተማረ ዓመት ከስድስት ወር ተቀመጠ። ጋልዮስም በአካይያ አገረ ገዥ በነበረ ጊዜ፥ አይሁድ በአንድ ልብ ሆነው በጳውሎስ ላይ ተነሡ፥ ወደ ፍርድ ወንበርም አምጥተው፦ ይህ ሕግን ተቃውሞ እግዚአብሔርን ያመልኩት ዘንድ ሰዎችን ያባብላል አሉ። ጳውሎስም አፉን ሊከፍት ባሰበ ጊዜ፥ ጋልዮስ አይሁድን፦ አይሁድ ሆይ፥ ዓመፅ ወይም ክፉ በደል በሆነ እንድታገሣችሁ በተገባኝ፤ ስለ ቃልና ስለ ስሞች ስለ ሕጋችሁም የምትከራከሩ ከሆነ ግን፥ ራሳችሁ ተጠንቀቁ እኔ በዚህ ነገር ፈራጅ እሆን ዘንድ አልፈቅድምና አላቸው። ከፍርድ ወንበርም ፊት አስወጣቸው። የግሪክ ሰዎችም ሁሉ የምኩራብ አለቃ ሶስቴንስን ይዘው በወንበሩ ፊት መቱት፤ በእነዚህም ነገሮች ጋልዮስ ግድ የለውም ነበር። ከዚህም በኋላ ጳውሎስ እጅግ ቀን ተቀምጦ ወንድሞቹንም ተሰናብቶ በመርከብ ወደ ሶርያ ሄደ፤ ስለትም ነበረበትና ራሱን በክንክራኦስ ተላጨ፤ ጵርስቅላና አቂላም ከእርሱ ጋር ነበሩ። ወደ ኤፌሶንም በደረሱ ጊዜ እነዚያን ከዚያ ተዋቸው፥ ራሱ ግን ወደ ምኵራብ ገብቶ ከአይሁድ ጋር ይነጋገር ነበር። እነርሱም ብዙ ጊዜ እንዲቀመጥላቸው ሲለምኑት እሺ አላለም፤ ነገር ግን ሲሰናበታቸው፦ የሚመጣውን በዓል በኢየሩሳሌም አደርግ ዘንድ ይገባኛል እግዚአብሔር ቢፈቅድ ግን ወደ እናንተ ደግሞ እመለሳለሁ አላቸው። ከኤፌሶንም በመርከብ ተነሣ። ወደ ቂሣርያም በደረሰ ጊዜ ወጥቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምታ ከሰጠ በኋላ ወደ አንጾኪያ ወረደ። ጥቂት ቀንም ቆይቶ ወጣ፥ ደቀ መዛሙርትንም ሁሉ እያጸና በገላትያ አገርና በፍርግያ በተራ አለፈ። በወገኑም የእስክንድርያ ሰው የሆነ ነገር አዋቂ የነበረ አጵሎስ የሚሉት አንድ አይሁዳዊ ሰው ወደ ኤፌሶን ወረደ፤ እርሱም በመጻሕፍት እውቀት የበረታ ነበረ። እርሱ የጌታን መንገድ የተማረ ነበረ፥ የዮሐንስንም ጥምቀት ብቻ አውቆ በመንፈስ ሲቃጠል ስለ ኢየሱስ ይናገርና በትክክል ያስተምር ነበር። እርሱም በምኵራብ ገልጦ ይናገር ጀመር። ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜም ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል ገለጡለት። እርሱም ወደ አካይያ ማለፍ በፈቀደ ጊዜ፥ ወንድሞቹ አጸናኑት፥ ይቀበሉትም ዘንድ ወደ ደቀ መዛሙርት ጻፉለት፤ በደረሰም ጊዜ አምነው የነበሩትን በጸጋ እጅግ ይጠቅማቸው ነበር፤ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደ ሆነ ከመጻሕፍት እየገለጠ ለአይሁድ በሁሉ ፊት በጽኑ ያስረዳቸው ነበርና።

ሐዋርያት ሥራ 18:1-28 አማ05 (አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም)

ከዚህ በኋላ ጳውሎስ ከአቴና ተነሥቶ ወደ ቆሮንቶስ ሄደ፤ እዚያ የጳንጦስ ተወላጅ የሆነውን አቂላ የሚባል አንድ አይሁዳዊ ሰው አገኘ፤ የሮም ንጉሠ ነገሥት ቀላውዴዎስ አይሁድ ሁሉ ከሮም እንዲወጡ አዞ ስለ ነበረ አቂላ ከሚስቱ ከጵርስቅላ ጋር ከኢጣልያ ገና መምጣቱ ነበር፤ ስለዚህ ጳውሎስ ወደ እነርሱ ሄዶ ተዋወቃቸው፤ የእርሱ ሥራ ልክ እንደ እነርሱ ድንኳን መስፋት ስለ ነበር ከእነርሱ ጋር ተቀምጦ አብሮአቸው ይሠራ ነበር። በየሰንበቱም በምኲራብ እየተገኘ ንግግር በማድረግ ለአይሁድና ለግሪኮች ያስረዳ ነበር። ሲላስና ጢሞቴዎስ ከመቄዶንያ በመጡ ጊዜ ጳውሎስ “ኢየሱስ መሲሕ ነው” በማለት ለአይሁድ በትጋት እየመሰከረ በማስተማር ጊዜውን ሁሉ ያሳልፍ ነበር። ነገር ግን አይሁድ በተቃወሙትና በሰደቡት ጊዜ የልብሱን ትቢያ አራግፎ “እንግዲህ ቢፈረድባችሁ በራሳችሁ ጥፋት ነው! እኔ ኀላፊነት የለብኝም፤ ከእንግዲህ ወዲህ ወደ አሕዛብ እሄዳለሁ!” አላቸው። ስለዚህ ከእነርሱ ተለይቶ ቲቶስ ኢዮስጦስ ወደተባለው ሰው ቤት ሄደ፤ ይህ ሰው እግዚአብሔርን የሚያመልክ ነበር፤ ቤቱም በምኲራብ አጠገብ ነበር። ቀርስጶስ የሚባል የምኲራብ አለቃ ከቤተሰቡ ሁሉ ጋር በጌታ አመነ፤ ብዙ የቆሮንቶስ ሰዎችም ጳውሎስ ሲናገር ሰምተው አመኑና ተጠመቁ። ጌታም ጳውሎስን ሌሊት በራእይ እንዲህ አለው፦ “አትፍራ፤ ተናገር፤ ዝም አትበል፤ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፤ በዚህች ከተማ ብዙ ሰዎች አሉኝና ጒዳት ሊያደርስብህ የሚችል ማንም የለም።” ስለዚህ ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ቃል ለሕዝቡ እያስተማረ አንድ ዓመት ተኩል እዚያ ቈየ። ጋልዮስ የአካይያ ገዢ ሆኖ በተሾመ ጊዜ አይሁድ በአንድነት ተባብረው በጳውሎስ ላይ ተነሡ፤ ወደ ፍርድ ሸንጎ ወሰዱትና፥ “ይህ ሰው ሕግን በሚቃወም መንገድ ሰዎች እግዚአብሔርን እንዲያመልኩ ያደርጋል!” አሉ። ጳውሎስ መልስ ለመስጠት ተዘጋጅቶ ሳለ ጋልዮስ አይሁድን እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ የአይሁድ ወገኖች! በደል ወይም ከባድ ወንጀል ተፈጽሞባችሁ ቢሆን ኖሮ ክሳችሁን በትዕግሥት በሰማሁ ነበር፤ ነገር ግን ስለ ቃላትና ስለ ስሞች ስለ ሕጋችሁም የምትከራከሩ ከሆነ የራሳችሁ ጉዳይ ነው፤ እኔ በእነዚህ ነገሮች ላይ መፍረድ አልፈልግም።” እንዲህም ብሎ ከፍርድ ሸንጎው አስወጣቸው። በዚህ ጊዜ ሁሉም የምኲራብ አለቃውን ሶስቴንስን ይዘው በሸንጎው ፊት ደበደቡት፤ ይህ ሁሉ ሲሆን ጋልዮስ ደንታ አልነበረውም። ጳውሎስ ከወንድሞች ጋር ብዙ ቀኖች በቆሮንቶስ ከቈየ በኋላ ተሰናብቶአቸው ወደ ሶርያ ሄደ፤ ጵርስቅላና አቂላም ከእርሱ ጋር ነበሩ፤ ነገር ግን ስለት ስለ ነበረበት ከመሄዱ በፊት ክንክሪያ በሚባል ቦታ ራሱን ተላጨ። ወደ ኤፌሶን በደረሱ ጊዜ ጵርስቅላንና አቂላን እዚያ ተዋቸው፤ እርሱ ግን ወደ ምኲራብ ገብቶ ለአይሁድ ንግግር ያደርግ ነበር። ረዘም ላለ ጊዜ ከእነርሱ ጋር እንዲቈይ ቢለምኑትም እሺ አላላቸውም። ነገር ግን “የእግዚአብሔር ፈቃድ ቢሆን ሌላ ጊዜ ወደ እናንተ ተመልሼ እመጣለሁ” አላቸውና ከኤፌሶን በመርከብ ተሳፍሮ ሄደ። ወደ ቂሳርያም በደረሰ ጊዜ ከዚያ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ ለቤተ ክርስቲያን ሰዎች ሰላምታ ከሰጠ በኋላ ተመልሶ ወደ አንጾኪያ ወረደ። እዚያም ጥቂት ጊዜ ቈየ፤ ከዚህ በኋላ በገላትያና በፍርግያ ምድር ከቦታ ወደ ቦታ እየተዘዋወረ አማኞችን አበረታታ። የእስክንድርያ ተወላጅ የሆነ አጵሎስ የተባለ አንድ አይሁዳዊ ወደ ኤፌሶን መጣ፤ እርሱ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጠንቅቆ የተማረና ጥሩ የአነጋገር ችሎታ ያለው ሰው ነበረ። ስለ ጌታ መንገድ የተማረና በመንፈስም የተቃጠለ ሆኖ ስለ ኢየሱስ በትክክል ይሰብክና ያስተምር ነበር፤ ይሁን እንጂ እርሱ የሚያውቀው የዮሐንስን ጥምቀት ብቻ ነበር። እርሱ በድፍረት በምኲራብ መናገር ጀመረ፤ ነገር ግን ጵርስቅላና አቂላ በሰሙት ጊዜ ወደ ቤታቸው ወሰዱትና የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል አብራርተው ገለጡለት። አጵሎስ ወደ አካይያ ለመሄድ ባሰበ ጊዜ ወንድሞች አሳቡን ደገፉ፤ በአካይያ ያሉ ወንድሞች በመልካም ሁኔታ እንዲቀበሉትም ደብዳቤ ጻፉለት። እዚያም በደረሰ ጊዜ በእግዚአብሔር ጸጋ አማኞች ለመሆን የበቁትን በጣም ረዳቸው። ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን በቅዱሳት መጻሕፍት ቃል እያስረዳ በብርቱ ክርክር አይሁድን ይረታቸው ነበር።

ሐዋርያት ሥራ 18:1-28 መቅካእኤ (መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ))

ከዚህም በኋላ ጳውሎስ ከአቴና ወጥቶ ወደ ቆሮንቶስ መጣ። በወገኑም የጳንጦስ ሰው የሚሆን አቂላ የሚሉትን አንድ አይሁዳዊ አገኘ፤ እርሱም ከጥቂት ጊዜ በፊት ከሚስቱ ከጵርስቅላ ጋር ከኢጣልያ መጥቶ ነበር፤ አይሁድ ከሮሜ ይወጡ ዘንድ ቀላውዴዎስ አዞ ነበርና፤ ወደ እነርሱ ቀረበ፤ ሥራቸውም አንድ ስለ ነበረ በእነርሱ ዘንድ ተቀምጦ በአንድ ላይ ሠሩ፤ ሥራቸው ድንኳን መስፋት ነበረና። በየሰንበቱም ሁሉ በምኵራብ ይነጋገር ነበር፤ አይሁድንና የግሪክንም ሰዎች ያስረዳ ነበር። ሲላስና ጢሞቴዎስም ከመቄዶንያ በወረዱ ጊዜ፥ ጳውሎስ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ ለአይሁድ እየመሰከረ ለቃሉ ይተጋ ነበር። ነገር ግን በተቃወሙትና በተሳደቡ ጊዜ፥ ልብሱን እያራገፈ “ደማችሁ በራሳችሁ ነው፤ እኔ ንጹሕ ነኝ፤ ከእንግዲህ ወዲህ ወደ አሕዛብ እሄዳለሁ፤” አላቸው። ከዚያም ወጥቶ ኢዮስጦስ ወደሚባል እግዚአብሔርን ወደሚያመልክ ሰው ቤት ገባ፤ ቤቱም በምኵራብ አጠገብ ነበረ። የምኵራብ አለቃ ቀርስጶስም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር በጌታ አመነ፤ ከቆሮንቶስ ሰዎችም ብዙ በሰሙ ጊዜ አምነው ተጠመቁ። ጌታም ሌሊት በራእይ ጳውሎስን “እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፤ ማንም ክፉ ሊያደርግብህ የሚነሣብህ የለምና አትፍራ፤ ነገር ግን ተናገር፤ ዝምም አትበል፤ በዚህ ከተማ ብዙ ሕዝብ አሉኝና፤” አለው። በመካከላቸውም የእግዚአብሔርን ቃል እያስተማረ ዓመት ከስድስት ወር ተቀመጠ። ጋልዮስም በአካይያ አገረ ገዥ በነበረ ጊዜ፥ አይሁድ በአንድ ልብ ሆነው በጳውሎስ ላይ ተነሡ፤ ወደ ፍርድ ወንበርም አምጥተው “ይህ ሕግን ተቃውሞ እግዚአብሔርን ያመልኩት ዘንድ ሰዎችን ያባብላል፤” አሉ። ጳውሎስም አፉን ሊከፍት ባሰበ ጊዜ፥ ጋልዮስ አይሁድን “አይሁድ ሆይ! ዐመፅ ወይም ክፉ በደል በሆነ እንድታገሣችሁ በተገባኝ፤ ስለ ቃልና ስለ ስሞች ስለ ሕጋችሁም የምትከራከሩ ከሆነ ግን፥ ራሳችሁ ተጠንቀቁ፤ እኔ በዚህ ነገር ፈራጅ እሆን ዘንድ አልፈቅድምና፤” አላቸው። ከፍርድ ወንበርም ፊት አስወጣቸው። የግሪክ ሰዎችም ሁሉ የምኵራብ አለቃ ሶስቴንስን ይዘው በወንበሩ ፊት መቱት፤ በእነዚህም ነገሮች ጋልዮስ ግድ የለውም ነበር። ከዚህም በኋላ ጳውሎስ እጅግ ቀን ተቀምጦ ወንድሞችንም ተሰናብቶ በመርከብ ወደ ሶርያ ሄደ፤ ስለትም ነበረበትና ራሱን በክንክራኦስ ተላጨ፤ ጵርስቅላና አቂላም ከእርሱ ጋር ነበሩ። ወደ ኤፌሶንም በደረሱ ጊዜ እነዚያን ከዚያ ተዋቸው፤ ራሱ ግን ወደ ምኵራብ ገብቶ ከአይሁድ ጋር ይነጋገር ነበር። እነርሱም ብዙ ጊዜ እንዲቀመጥላቸው ሲለምኑት እሺ አላለም፤ ነገር ግን ሲሰናበታቸው “የሚመጣውን በዓል በኢየሩሳሌም አደርግ ዘንድ ይገባኛል እግዚአብሔር ቢፈቅድ ግን ወደ እናንተ ደግሞ እመለሳለሁ፤” አላቸው። ከኤፌሶንም በመርከብ ተነሣ። ወደ ቂሣርያም በደረሰ ጊዜ ወጥቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምታ ከሰጠ በኋላ ወደ አንጾኪያ ወረደ። ጥቂት ቀንም ቆይቶ ወጣ፤ ደቀ መዛሙርትንም ሁሉ እያጸና በገላትያ አገርና በፍርግያ በተራ አለፈ። በወገኑም የእስክንድርያ ሰው የሆነ ነገር አዋቂ የነበረ አጵሎስ የሚሉት አንድ አይሁዳዊ ሰው ወደ ኤፌሶን ወረደ፤ እርሱም በመጻሕፍት እውቀት የበረታ ነበረ። እርሱ የጌታን መንገድ የተማረ ነበረ፤ የዮሐንስንም ጥምቀት ብቻ አውቆ በመንፈስ ሲቃጠል ስለ ኢየሱስ ይናገርና በትክክል ያስተምር ነበር። እርሱም በምኵራብ ገልጦ ይናገር ጀመር። ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜም ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል ገለጡለት። እርሱም ወደ አካይያ ማለፍ በፈቀደ ጊዜ፥ ወንድሞቹ አጸናኑት፤ ይቀበሉትም ዘንድ ወደ ደቀ መዛሙርት ጻፉለት፤ በደረሰም ጊዜ አምነው የነበሩትን በጸጋ እጅግ ይጠቅማቸው ነበር፤ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ ከመጻሕፍት እየገለጠ ለአይሁድ በሁሉ ፊት በጽኑ ያስረዳቸው ነበርና።