1 ሳሙኤል 1:1-6
1 ሳሙኤል 1:1-6 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ) (አማ2000)
በተራራማው በኤፍሬም ሀገር ከአርማቴም መሴፋ የሆነ አንድ ሰው ነበረ። ስሙም፥ የናሲብ ልጅ የቴቆ ልጅ፥ የኤልዩ ልጅ ፥ የኢያርምያል ልጅ፥ ኤፍራታዊው ሕልቃና ነበረ። ሁለትም ሚስቶች ነበሩት፤ የአንዲቱ ስም ሐና፥ የሁለተኛዪቱም ስም ፍናና ነበረ፤ ለፍናናም ልጆች ነበሩአት፤ ለሐና ግን ልጆች አልነበሩአትም። ያም ሰው በሴሎ ይሰግድ ዘንድ፥ ለሠራዊት ጌታም ለእግዚአብሔር ይሠዋ ዘንድ ከከተማው ከአርማቴም በየዓመቱ ይወጣ ነበር። የእግዚአብሔርም ካህናት ሁለቱ የዔሊ ልጆች አፍኒንና ፊንሐስ በዚያ ነበሩ። ሕልቃናም የሚሠዋበት ቀን በደረሰ ጊዜ ለሚስቱ ለፍናናና ለልጆችዋ ሁሉ ዕድል ፋንታቸውን ሰጣቸዉ። ለሐናም ልጅ ስላልነበራት አንድ ዕድል ፋንታ ሰጣት፤ ሕልቃናም ከዚያችኛይቱ ይልቅ ሐናን ይወድድ ነበር። እግዚአብሔር ግን ማኅፀንዋን ዘግቶ ነበር። እንደ መከራዋና እንደ ኀዘንዋም እግዚአብሔር ልጅ አልሰጣትም ነበር። ስለዚህም ታዝን ነበር። እግዚአብሔር ማኅፀንዋን ዘግትዋልና፥ ልጆችንም አልሰጣትምና።
1 ሳሙኤል 1:1-6 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
በተራራማው በኤፍሬም አገር በአርማቴም መሴፋ የሚኖር ሕልቃና የተባለ አንድ ሰው ነበረ፤ እርሱም ኤፍሬማዊ ሲሆን፣ የኤያሬምኤል ልጅ፣ የኢሊዩ ልጅ፣ የቶሑ ልጅ፣ የናሲብ ልጅ፣ ነበረ። እርሱም አንዲቱ ሐና፣ ሌላዪቱ ፍናና የተባሉ ሁለት ሚስቶች ነበሩት፤ ፍናና ልጆች ሲኖሯት፣ ሐና ግን ምንም ልጅ አልነበራትም። ያም ሰው ለሰራዊት ጌታ ለእግዚአብሔር ለመስገድና መሥዋዕት ለመሠዋት በየዓመቱ ከሚኖርበት ከተማ ወደ ሴሎ ይወጣ ነበር። በዚያም ሁለቱ የዔሊ ልጆች አፍኒንና ፊንሐስ የእግዚአብሔር ካህናት ነበሩ። ሕልቃና ወደ ሴሎ ሄዶ መሥዋዕት የሚሠዋበት ወቅት በደረሰ ጊዜ ሁሉ፣ ለሚስቱ ለፍናና እንዲሁም ለወንዶችና ለሴቶች ልጆቿ ሁሉ ከሥጋው ድርሻቸውን ይሰጣቸው ነበር። ሐናን ግን ይወድዳት ስለ ነበር፣ ዕጥፍ ድርሻ ይሰጣት ነበር፤ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር ማሕፀኗን ዘግቶት ነበር። እግዚአብሔር ማሕፀኗን ስለ ዘጋም ጣውንቷ ታስቈጣት፣ ታበሳጫትም ነበር።
1 ሳሙኤል 1:1-6 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
በተራራማው በኤፍሬም አገር ከአርማቴም መሴፋ የሆነ ስሙ ሕልቃና የተባለ ኤፍሬማዊ ሰው ነበረ፥ እርሱም የኢያሬምኤል ልጅ የኢሊዮ ልጅ የቶሑ ልጅ የናሲብ ልጅ ነበረ። ሁለትም ሚስቶች ነበሩት የአንዲቱ ስም ሐና የሁለተኛይቱም ስም ፍናና ነበረ፥ ለፍናናም ልጆች ነበሩአት፥ ለሐና ግን ልጅ አልነበራትም። ያም ሰው በሴሎ ይሰግድ ዘንድ ለሠራዊት ጌታም ለእግዚአብሔር ይሠዋ ዘንድ ከከተማው በየዓመቱ ይወጣ ነበር። የእግዚአብሔርም ካህናት ሁለቱ የዔሊ ልጆች አፍኒንና ፊንሐስ በዚያ ነበሩ። ሕልቃና የሚሠዋበት ቀን በደረሰ ጊዜም ለሚስቱ ለፍናና ለወንዶችና ለሴቶች ልጆችዋ ሁሉ እድል ፈንታቸውን ሰጣቸው። ሐናንም ይወድድ ነበርና ለሐና ሁለት እጥፍ እድል ፈንታ ሰጣት፥ እግዚአብሔር ግን ማኅፀንዋን ዘግቶ ነበርና ጣውንትዋ ታስቆጣት ታበሳጫትም ነበር።
1 ሳሙኤል 1:1-6 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
በኮረብታማው በኤፍሬም አገር ራማ ተብላ በምትጠራ ትንሽ ከተማ የሚኖር ትውልዱ ከኤፍሬም ነገድ የሆነ፥ ሕልቃና ተብሎ የሚጠራ አንድ ሰው ነበር፤ እርሱም የይሮሐም ልጅ የኤሊሁ የልጅ ልጅ ሲሆን፥ ኤሊሁ ደግሞ የቶሑ ልጅ የጹፍ የልጅ ልጅ ነበር፤ ሕልቃናም ሐናና ፍኒና ተብለው የሚጠሩ ሁለት ሚስቶች ነበሩት፤ ፍኒና ልጆች ነበሩአት፤ ሐና ግን አንድም ልጅ አልነበራትም፤ ሕልቃና በየዓመቱ ለሠራዊት ጌታ ለእግዚአብሔር ለመስገድና መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ሴሎ ይሄድ ነበር፤ በዚያም ዘመን ሖፍኒና ፊንሐስ ተብለው የሚጠሩት የዔሊ ልጆች የእግዚአብሔር ካህናት ሆነው በሴሎ ያገለግሉ ነበር። ሕልቃና መሥዋዕቱን በሚያቀርብበት ጊዜ ሁሉ ከመሥዋዕቱ ሥጋ አንድ ድርሻ ለጵኒና ይሰጣል፤ እንዲሁም ለወንዶችና ለሴቶች ልጆችዋ ለእያንዳንዳቸው አንዳንድ ድርሻ ያድላል፤ ሐናን ይወዳት ስለ ነበር እጥፍ ድርሻ ይሰጣት ነበር፤ ቢሆንም እግዚአብሔር ልጅ ስላልሰጣት መኻን ነበረች፤ እግዚአብሔርም ልጅ ስላልሰጣት ጣውንትዋ ጵኒና ሐናን የሚያስቈጣ ነገር በመፈለግ ታበሳጫት ነበር፤
1 ሳሙኤል 1:1-6 መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) (መቅካእኤ)
በተራራማው በኤፍሬም አገር በአርማቴም መሴፋ የሚኖር ሕልቃና የተባለ አንድ ሰው ነበረ፤ እርሱም የይሮሐም ልጅ፥ የኤሊዩ ልጅ፥ የቶሑ ልጅ፥ የናሲብ ልጅ ሲሆን ከኤፍሬም ነገድ ነበረ። እርሱም ሁለት ሚስቶች ነበሩት፤ ስማቸውም አንዲቱ ሐና፥ ሁለተኛዪቱም ጵኒና ነበር። ጵኒና ልጆች ነበሯት፤ ሐና ግን ምንም ልጅ አልነበራትም። ያም ሰው በየዓመቱ ለሠራዊት ጌታ ለመስገድና መሥዋዕት ለመሠዋት ከሚኖርበት ከተማ ወደ ሴሎ ይወጣ ነበር። በዚያም ሁለቱ የዔሊ ልጆች ሖፍኒና ፊንሐስ የጌታ ካህናት ነበሩ። ሕልቃና መሥዋዕት የሚሠዋበት ወቅት በደረሰ ጊዜ ሁሉ፥ ለሚስቱ ለጵኒና እንዲሁም ለወንዶችና ለሴቶች ልጆችዋ ሁሉ ድርሻቸውን ይሰጣቸው ነበር። ሐናንም ይወዳት ስለ ነበር ዕጥፍ ድርሻ ይሰጣት ነበር፤ ይሁን እንጂ ጌታ ማሕፀኗን ዘግቶት ነበር። ጌታ ማሕፀኗን ስለዘጋም ጣውንቷ ሆን ብላ ታስቆጣት፥ ታበሳጫትም ነበር።