መጽሐፈ ምሳሌ 9:1-18

መጽሐፈ ምሳሌ 9:1-18 አማ2000

ጥበብ ለራስዋ ቤቷን ሠራች፥ ሰባቱንም ምሰሶዎችዋን አቆመች። ፍሪዳዋን አረደች፥ የወይን ጠጅዋንም በማድጋዋ ጨመረች። ማዕድዋን አዘጋጀች። አገልጋዮችዋን ልካ በከፍተኛ ዐዋጅ ወደ ማዕድዋ ጠራች። እንዲህም አለች፦ “አላዋቂ የሆነ ወደ እኔ ይምጣ፤” አእምሮ የጎደላቸውንም እንዲህ አለች፦ “ኑ፥ እንጀራዬን ብሉ፥ የጠመቅሁላችሁን የወይን ጠጅም ጠጡ። ስንፍናን ትታችሁ በሕይወት ኑሩ፥ በሕይወትም ትኖሩ ዘንድ ዕውቀትን ፈልጉ፥ በመረዳትም ዕውቀትን አቅኑ።” ክፉዎችን የሚያስተምር ለራሱ ውርደትን ይቀበላል፥ ኃጥእንም የሚገሥጽ ራሱን ያዋርዳል። ሰነፎችን አትገሥጽ እንዳይጠሉህ፥ ጠቢብን ገሥጽ ይወድድህማል። ለጠቢብ ሰው ትምህርትን ስጠው፥ ጥበብንም ያበዛል፤ ጻድቅንም አስተምረው፥ ዕውቀትንም ያበዛል። የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ የቅዱሳንም ምክር ዕውቀት ነው፥ ሕግንም ማወቅ ለልብ ደግ ነው። በዚህ ሥርዐት ብዙ ዘመን ትኖራለህ፥ የሕይወትህም ዓመታት ይጨመሩልሃል። ልጄ ሆይ፥ ለራስህ ጠቢብ ብትሆን ለባልንጀራህም ጠቢብ ትሆናለህ፥ ክፉም ብትሆን ክፋትን ለብቻህ ትሸከማለህ። ሐሰትን የሚያዘጋጅ ሰው ነፋሳትን እንደሚያዘጋጅ ሰው ይመስላል። እርሱም የሚበርር ዎፍን እንደሚከተል ነው። የወይኑ ቦታ መንገዱን ተወ፤ የሚሰማራባትን መንገድ ዘነጋ፤ ወደ ምድረ በዳ ይሄዳል፥ ለጥም ወደ ተሠራች ምድርም ይሄዳል፤ የማያፈራና የማይጠቅም ገንዘብንም በእጁ ይሰበስባል። ሰነፍና ነዝናዛ፥ እንጀራንም ያጣች ሴት ኀፍረትን የማታውቅ ትሆናለች። በቤቷ ደጅ በአደባባይ በወንበር ላይ በግልጥ ተቀምጣ፥ በመንገድ የሚያልፉትን አካሄዳቸውንም ያቀኑትን ትጠራለች። ከእነርሱ ወገን ሰነፍ የሆነው ወደ እርሷ ይቀርባል። አእምሮ የጐደለውንም እንዲህ ብላ ታዝዘዋለች፦ “የተሸሸገ እንጀራን አሰማምረህ ዳስስ። ጣፋጭ የስርቆት ውኃንም ጠጣ፥” ነገር ግን እርሱ ከኀያላን ወገን በእርሷ ዘንድ የሚጠፉ እንዳሉ፥ የሲኦል ወጥመድም በቤቷ እንደሚገኝ አያውቅም። ነገር ግን ፈጥነህ ሂድ፥ በቦታዋም አትዘግይ፥ የባዕድን ውኃ እንደምትሻገር በዐይንህ ወደ እርሷ መመልከትን አታዘውትር። ከባዕድ ውኃ ራቅ፥ ብዙ ዘመን ትኖር ዘንድ ከባዕድ ምንጭ ውኃ አትጠጣ። የሕይወትህም ዓመታት ይጨመሩልሃል።