የሐዋርያት ሥራ 9:26-43
የሐዋርያት ሥራ 9:26-43 አማ2000
ሳውልም ወደ ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ ሊገናኛቸው ደቀ መዛሙርትን ፈለጋቸው። ሁሉም ፈሩት፤ የጌታችን ደቀ መዝሙር እንደ ሆነ አላመኑትም ነበርና። በርናባስም አግኝቶ ወደ ሐዋርያት ወሰደው፤ ጌታችንም በመንገድ እንደ ተገለጠለትና እንደ አነጋገረው፥ በደማስቆም በኢየሱስ ስም እንደ አስተማረ ነገራቸው። በኢየሩሳሌምም አብሮአቸው ይገባና ይወጣ ነበረ፤ በጌታችን በኢየሱስ ስምም በግልጥ ያስተምር ነበር። ከግሪክ ሀገር መጥተው የነበሩትንም አይሁድ ይከራከራቸው ነበር፤ እነርሱም ደግሞ ሊገድሉት ፈለጉ። ወንድሞችም ይህን ባወቁ ጊዜ ወደ ቂሳርያ አወረዱት፤ ከዚያም ወደ ጠርሴስ ላኩት። በይሁዳ፥ በሰማርያና በገሊላ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በሰላም ኖሩ፤ ታነጹም፤ እግዚአብሔርንም በመፍራት ጸንተው ኖሩ፤ ሕዝቡም በመንፈስ ቅዱስ አጽናኝነት በዙ። ከዚህም በኋላ ጴጥሮስ በየቦታዉ ሲዘዋወር በልዳ ወደሚኖሩት ቅዱሳን ዘንድ ደረሰ። በዚያም ኤንያ የተሰኘ ሰውን አገኘ፤ እርሱም ታሞ በአልጋ ከተኛ ስምንት ዓመት ሆኖት ነበረ፤ ሽባ ነበርና። ጴጥሮስም፥ “ኤንያ ሆይ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ይፈውስህ፤ ተነሥና አልጋህን አንጥፍ” አለው፤ ያንጊዜም ተነሣ። በልዳና በሳሮና የሚኖሩም ሁሉ እርሱን አይተው ወደ ጌታችን ተመለሱ። በኢዮጴ ሀገርም ጣቢታ የምትባል አንዲት ደቀ መዝሙር ነበረች፤ በትርጓሜውም ዶርቃስ ይሉአታል፤ ፌቆ ማለት ነው፤ እርስዋም ብዙ ደጋግ ሥራ ትሠራ ነበር፤ ምጽዋትም ትሰጥ ነበር። ያንጊዜም ታማ ሞተችና በድንዋን አጥበው በሰገነት አስተኙአት። ልዳም ለኢዮጴ ቅርብ ነበርና ደቀ መዛሙርት ጴጥሮስ በዚያ እንዳለ ሰምተው ወደ እነርሱ መምጣት እንዳይዘገይ ይማልዱት ዘንድ ሁለት ሰዎችን ወደ እርሱ ላኩ። ጴጥሮስም ተነሥቶ አብሮአቸው ሄደ፤ በደረሰም ጊዜ ወደ ሰገነት አወጡት፤ ባልቴቶችም ሁሉ ወደ እርሱ መጥተው በፊቱ ቆሙ፤ ያለቅሱላትም ነበር፤ ዶርቃስም በሕይወት ሳለች የሠራችውን ቀሚሱንና መጐናጸፊያውን አሳዩት። ጴጥሮስም ሁሉን ካስወጣ በኋላ ተንበርክኮ ጸለየ፤ ወደ በድንዋም መለስ ብሎ፥ “ጣቢታ ሆይ፥ ተነሽ” አላት፤ እርስዋም ዐይኖችዋን ገለጠች፤ ያንጊዜም ጴጥሮስን አየችው፤ ቀና ብላም ተቀመጠች። እጁንም ለእርስዋ ሰጥቶ አስነሣት፤ ቅዱሳንንና ባልቴቶችንም ጠርቶ እርስዋን አድኖ ሰጣቸው። በኢዮጴም ያሉ ሁሉ ይህን ሰሙ፤ ብዙዎችም በጌታችን አመኑ። ጴጥሮስም በኢዮጴ በቍርበት ፋቂው በስምዖን ቤት ብዙ ቀን ተቀመጠ።

