በዳዊትም ዘመን ሦስት ዓመት ያህል በተከታታይ ራብ ሆነ፤ ዳዊትም የእግዚአብሔርን ቃል ጠየቀ። እግዚአብሔርም አለ፥ “የገባዖንን ሰዎች ስለ ገደለ በሳኦልና በቤቱ ላይ ደም አለበት፥” ንጉሡ ዳዊትም የገባዖንን ሰዎች ጠራ፤ የገባዖን ሰዎችም ከአሞራውያን የተረፉ ነበሩ እንጂ ከእስራኤል ልጆች ወገን አልነበሩም፤ የእስራኤልም ልጆች ምለውላቸው ነበር፤ ሳኦል ግን ለእስራኤል ልጆችና ለይሁዳ ስለ ቀና ሊገድላቸው ወድዶ ነበር። ዳዊትም የገባዖንን ሰዎች፥ “የእግዚአብሔርን ርስት ትባርኩ ዘንድ ምን ላድርግላችሁ? ማስተስረያውስ ምንድን ነው?” አላቸው። የገባዖን ሰዎችም፥ “ከሳኦልና ከቤቱ ወርቅ ወይም ብር አንፈልግም፤ ከእስራኤልም ወገን እኛ የምንገድለው የለም” አሉት። እርሱም፥ “ምን ትላላችሁ? ተናገሩ፤ እኔም አደርግላችኋለሁ” አላቸው፤ እነርሱም ለንጉሡ አሉት፥ “በእኛ ላይ ክፉ ያደረገውን፥ ያሳደደንንና ሊያጠፋን ያሰበውን ሰው እናጥፋው፤ እርሱም በእስራኤል ዳርቻ እንዳይቆም እናደርገዋለን። ከልጆቹ ሰባት ሰዎች ስጠንና ከእግዚአብሔር በተመረጠው በሳኦል ሀገር በገባዖን ለእግዚአብሔር እንሠቅላቸዋለን።” ንጉሡም፥ “እሰጣችኋለሁ” አለ። ንጉሡም በእነርሱ መካከል፥ በዳዊትና በሳኦል ልጅ በዮናታን መካከል ስለ ነበረው ስለ እግዚአብሔር መሐላ የሳኦልን ልጅ የዮናታንን ልጅ ሜምፌቡስቴን ራራለት። ንጉሡም ለሳኦል የወለደቻቸውን የኢዮሄልን ልጅ የሩጻፋን ሁለቱን ልጆች ሄርሞንስቴንና ሜምፌቡስቴን፥ ለመሓላታዊውም ለቤርዜሊ ልጅ ለኤስድራ የወለደቻቸውን የሳኦልን ልጅ የሜሮብን አምስቱን ልጆች ወሰደ፤ በገባዖንም ሰዎች እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፤ በእግዚአብሔርም ፊት በተራራው ላይ ሰቀሏቸው። ሰባቱም በአንድነት ወደቁ፤ እህል በሚታጨድበትም ወራት በገብሱ መከር መጀመሪያ ተገደሉ። የኢዮሔል ልጅ ሩጻፋም ማቅ ወስዳ ከመከር ወራት ጀምሮ ዝናብ ከሰማይ እስኪዘንብ ድረስ በድንጋይ ላይ ዘረጋችው፤ በቀንም የሰማይ ወፎች፥ በሌሊትም የዱር አራዊት ያርፉባቸው ዘንድ አልተወችም። የሳኦልም ዕቅብት የኢዮሔል ልጅ ሩጻፋ ያደረገችውን ለዳዊት ነገሩት። ዳዊትም ሄደ፤ ሳአልንም በጌላቡሄ በገደሉት ጊዜ ፍልስጥኤማውያን ከሰቀሉአቸው ስፍራ ከቤትሳን አደባባይ ከሰረቁት ከኢያቤስ ገለዓድ ሰዎች የሳኦልን አጥንትና የልጁን የዮናታንን አጥንት ወሰደ። ከዚያም የሳኦልን አጥንትና የልጁን የዮናታንን አጥንት አመጣ፤ የተሰቀሉትንም ሰዎች አጥንት ሰበሰቡ። የሳኦልን አጥንትና የልጁን የዮናታንን አጥንት፥ የተሰቀሉትንም ሰዎች አጥንት በብንያም በአባቱ በቂስ መቃብር አጠገብ ቀበሩአቸው፤ ንጉሡም ያዘዘውን ሁሉ አደረጉ። ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ምድርን ሰማት።
መጽሐፈ ሳሙኤል ካልእ 21 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: መጽሐፈ ሳሙኤል ካልእ 21:1-14
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች