ሕግና ባህልን በሚመለከት ጉዳይ፥ ብልኅ አማካሪዎችን መጠየቅ በንጉሡ ዘንድ የተለመደ ነገር ስለ ነበር፥ በዚህም ጊዜ ምን ማድረግ እንደሚገባው ይመክሩት ዘንድ አማካሪዎቹን አስጠራ። ዘወትር የሚያማክሩትም ካርሸና፥ ሼታር፥ አድማታ፥ ታርሺሽ፥ ሜሬስ፥ ማርሰናና መሙካን ተብለው የሚጠሩ በመንግሥቱ አመራር ውስጥ ከፍተኛ ሥልጣን ያላቸው ሰባቱ የፋርስና የሜዶን ሹማምንት ነበሩ። ንጉሡም እነዚህን አማካሪዎች “እኔ ንጉሥ አርጤክስስ ንግሥት አስጢንን ያመጡ ዘንድ በማዘዝ አገልጋዮቼን ብልክባት እርስዋ እምቢ ብላ ቀርታለች! ታዲያ፥ በእርስዋ ላይ መወሰድ ስለሚገባው እርምጃ ሕጉ ምን ይላል?” ሲል ጠየቃቸው። ከዚህ በኋላ ከአማካሪዎቹ አንዱ የሆነው መሙካን እንዲህ ሲል የውሳኔ ሐሳብ አቀረበ፤ “በመሠረቱ ንግሥት አስጢን ያዋረደችው ንጉሡን ብቻ ሳይሆን ባለሟሎቹ የሆኑትን ባለሥልጣኖችና እንዲያውም በንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ግዛት ውስጥ ያሉትን ወንዶች ሁሉ ጭምር ነው። ከእንግዲህ ወዲህ በንጉሠ ነገሥቱ ግዛት ውስጥ የምትኖር ማንኛዋም ሴት፥ ንግሥት አስጢን ያደረገችውን ሁሉ ስትሰማ ባልዋን በንቀት ዐይን መመልከት ትጀምራለች፤ እነርሱም በበኩላቸው ‘ንጉሥ አርጤክስስ ንግሥት አስጢንን ወደ እርሱ እንድትመጣ ቢያስጠራት እምቢ ብላው ቀርታ የለምን?’ ይላሉ። የፋርስና የሜዶን መንግሥት ባለሥልጣኖች ሚስቶች ይህን ንግሥቲቱ የፈጸመችውን አሳፋሪ ድርጊት በሚሰሙበት ጊዜ ዛሬውኑ ፀሐይ ሳትጠልቅ በባሎቻቸው ላይ መዘባነን ይጀምራሉ፤ በየሀገሩ የሚገኙ ሚስቶችም ባሎቻቸውን ማክበርን ይተዋሉ፤ ባሎችም ከሚስቶቻቸው ጋር መጣላት ሊኖርባቸው ነው። ንጉሥ ሆይ! እንግዲህ መልካም ፈቃድህ ቢሆን፥ ንግሥት አስጢን ከእንግዲህ ወዲህ ወደ አንተ ፊት መቅረብ ከቶ እንዳይፈቀድላት የሚገልጥ ውሳኔህን በዐዋጅ አስተላልፍ፤ ይህም ውሳኔ ከቶ የማይለወጥ ሆኖ ለዘለዓለም ይጸና ዘንድ በፋርስና በሜዶን ሕግ ውስጥ እንዲመዘገብ ትእዛዝ አስተላልፍ፤ የአስጢንንም የንግሥትነት ማዕርግ ከእርስዋ ለተሻለች ለሌላ ሴት ስጥ። አንተ የምታስተላልፈውም ዐዋጅ እጅግ ታላቅ በሆነው በዚህ በንጉሠ ነገሥት መንግሥትህ ግዛት ሁሉ በይፋ በሚነገርበት ጊዜ እያንዳንድዋ ሴት ባለጸጋም ይሁን ወይም ድኻ ባልዋን በአክብሮት ትመለከታለች።” ንጉሡና ባለሟሎቹ የሆኑ ባለሥልጣኖች ሁሉ ይህን ሐሳብ በደስታ ተቀበሉት፤ ንጉሡም መሙካን ያቀረበውን ምክር በሥራ ላይ አዋለ። ስለዚህም ንጉሡ “እያንዳንዱ ባል የቤቱ አባወራ ሆኖ በአዛዥነት የመናገር መብቱ የተጠበቀ ይሁን!” የሚል ትእዛዝ በየቋንቋውና በየአጻጻፍ ሥርዓቱ ተዘጋጅቶ ወደያንዳንዱ አገር እንዲተላለፍ አደረገ።
መጽሐፈ አስቴር 1 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: መጽሐፈ አስቴር 1:13-22
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች